የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መዝሙራት ፔጅ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መዝሙራት ፔጅ This spiritual page is purely out of politics. The most important part of the gospel of God is being preached.

The gospel of God will be preached and the salvation of God will be proclaimed to all the world " we trust in god "

09/08/2023

❤ ?

❤ ?

❤ ?

ከዝሙት አጋንንት እና ከዝንየት በተጨማሪ በሕልመ ሌሊት የሚፈትነን አጋንንት የትኛው ነው?

❤ ?

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም

ሼር በማድረግ ለወዳጆ ያንሸራሽሯት

በትዕግስት እና በጥሞና አንብቡት!

የወለላይቱ እመቤት ልጆች መቼም ሱባኤ አይደል! በድካም ውስጥ ሆኜ ስለጻፍኩ የሐሳብ መደጋገም ካለ እያረማችሁ አንብቡት፡፡ በዚህ በሱባኤ የአጋንንት ውጊያ የሚበረታበት፣ሕልመ ሌሊት ደግሞ በተደጋጋሚ የሚከሰትበት ነው፡፡ የበጎ ነገር ጠላት አጋንንት እኛን ከመንፈሳዊ አገልግሎት እና ተገልጎሎት ለማሰናከል እኛ ላይ ዓይኑን ፈጠጥ፣ጥርሱን ገጠጥ የሚያደርግበት ጊዜ በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡

ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) የሚባለው አንድ ሰው ተኝቶ በሕልሙ ወንድን በሴት፣ ሴትን በወንድ አምሳል እንደ ገሐዱ በሚመስል ሩካቤ ሥጋ የሚታየንና ከሰውነታችን ፈሳሽ የሚወጣበት ሂደት ነው፡፡ ዝንየት የሚባለው ደግሞ በሕልመ ሌሊት የሚፈታተነን አጋንንት ነው፡፡ ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ወንድና ሴት ሳይል በማንኛውም ሰው ላይ በተለያየ ምክንያት ሊከሰት ይችላል፡፡

በሱባኤ ጊዜ ሕልመ ሌሊት ከመታን እለቱን ቤተ-ክርስትያን በተለይም ቤተ-መቅደስ መግባት፣ቅዱስ ቁርባን መቀበል፣ጸበል መጠመቅና መጠጣት፣ አንችልም፡፡ በማግስቱ ግን ሰውነታችንን ታጥበን፣ልብሳችንን ቀይረን ቤተ-ክርስትያን መግባት፣ቅዱስ ቁርባን መቀበል፣ጸበል መጠመቅና መጠጣት እንችላለ፡፡ እንደዚህ የምናደርገው አንደኛ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትእዛዝ ስለሆነ ነው፡፡

ሁለተኛ ቅድስት ለሆነችው እናት ቤተ-ክርስትያን ክብር ከመስጠት አንጻር ነው፡፡ እግዚአብሔር ሙሴንና አሮንን በዘሌዋውያን ምዕራፍ 15÷2 ላይ ‹‹ማንም ሰው ከሥጋው ፈሳሽ ነገር ቢወጣ፣ስለሚወጣው ነገር ርኩስ ነው›› ይልና እዛው ቁጥር 16 ላይ ‹‹ማንም ሰው ዘር ከእርሱ ቢወጣ፣ገላውን ሁሉ በውኃ ይታጠባል፣እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ነው›› ይላል፡፡ /ዘሌ 15÷16/

ተወዳጆች ሆይ ልብ በሉ ‹‹ማንም ሰው›› ነው እንጂ ወንድ ሴት፣ወጣት አዛውንት አይልም፡፡ ይህ የሚያሳየው ኦርቶዶክስ የሆነ በየትኛው ጾታ እና የእድሜ ክልል ያለ ሁሉ ሕልመ ሌሊት ከመታው እለቱን ሳይሆን ማግስቱን ነው ቤተ-ክርስትያን መግባት የሚችለው፡፡ ‹‹እስከ ማታ›› የሚለው ሕልመ ሌሊት ሲመታን ለአንድ ቀን ብቻ የተከለከልን መሆናችን ያስረዳል፡፡

መቼም ሕልመ ሌሊት የሚመታን ማታ ወይም ሌሊት ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ማታ ወይም ሌሊት ሕልመ ሌሊት ከመታው ቀኑን ውሎ እስከ ማታ ነው የሚረክሰው፡፡ ከማታ በኃላ ንፁህ ይሆናል፡፡

ወዳጆቼ አንዳንዶች ‹‹ሕልመ ሌሊት ከተመታችሁ እስከ ሦስት ቀን ቤተ-ክርስትያን መግባት አይቻልም›› ይላሉ፡፡ ይህንም ‹‹ማነው ያለው›› ስትሉ የፈረደባቸው ‹‹አባቶች›› ናቸው ይላሉ፡፡ ቅዱስ መጽሐፍም አባቶቻችንም የሚነግሩን እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቤተ-ክርስትያን የማንገበው ሩካቤ ሥጋ ስንፈጽም ብቻ ነው፡፡

ሕልመ ሌሊት መታን ማለት በቤት እና በቅጽረ ቤተ-ክርስትያን ሆኖ መጸለይ አይቻልም ማለት አይደለም፡፡ በሱባኤም ሆነን ሕልመ ሌሊት ቢመታን ሰውነታችን ታጥበት ሱባኤው መቀጠል እንጂ ማፍረስ የለብንም፡፡

❤ ?

ወዳጆቼ ሕልመ ሌሊት በራሱ ኃጢአት አይደለም፡፡ ግን ኃጢአት የሚሆንበት ሂደት አለው፡፡ አንድ ሰው በሕልሙ ሕልመ ሌሊት ቢመታው በዚህም ከሰውነቱ አባለ ዘር ይፈሳል፡፡ የአባለ ዘር መፍሰስ ኃጢአት የሚሆነው በራስ ፍቃድ ሲሆን ነው፡፡ ለምሳሌ ወዶ እና ፈቅዶ ግለ ወሲብ ሲፈጽም፣የወሲብ ፊልም በማየት ከሚመጣ የሰውነት ሙቀት ጋር ዘር ሲፈስ፣ከተቃራኒ ጾና ጋር በሚደረግ አልባል ንክኪና መሳሳም ነው፡፡

ሕልመ ሌሊት እላፊ በልቶ እና ጠጥቶ ከሚመጣ የሥጋ ፈተና ከሆነ ኃጢአት ይሆንበታል፡፡ ቅድስናን የሚያጎድል በመሆኑ የኃጢአተኝነት ስሜት እንዲጫነን ያደርገናል፡፡ ግን አንድ ሰውን ሕልመ ሌሊት ቢመታው ኃጢአት የሚሆንበት ሂደት አለ፡፡ ይህም አንድን ሰው ሕልመ ሌሊት ሲመታው ማለትም አጋንንቱ በሚያውቃት ሴት ተመስሎ በተኛበት ተገናኝቶት ዘሩን ቢያስፈስሰው የዚህ ችግር ሰለባ የሆነው ሰው በተፈጠረው ነገር ለምሳሌ ሴቷን እያሰበ፣ በሕልሙ ያየውን እያሰበ የሚደሰት፣ በሕልሙ የተፈጠረውን ግንኙነት በምልሰት እያየ ደስታን ካጣጣመ ኃጢአት ነው፡፡

ምክንያቱም ይሁዳ በመልእክቱ ‹‹እያለሙ ሥጋቸውን ያስደስታሉ›› ብሏልና፡፡ /ይሁ 1÷8/ በሕልማችን የተፈጠረውን ሕልመ ሌሊት በምልሰት በማየት እና በማሰብ መደሰት ሳይሆን መጸጸት መቆጨት ካልተሰማን ኃጢአት ነው የሚሆንብን፡፡

ወዳጆቼ የአጋንንት የረከሰ ሐሳብ በሕልማችን እየተከሰተ ሕልመ ሌሊት ሲያጋጥመን የተፈጠረውን ክስተት በጸጸት አጋንንቱን ልናሳፍረው ይገባል እንጂ የሆነውን እንደ በጎ ነገር ልንቀበለው አይገባም፡፡ ይህ እሳቤያችን ከፈጣሪ መለኮታዊ እርዳታ እንድናገኝ ይረዳናል፡፡ የማንቆጭ፣የማንጸጸት ከሆነ የዝንየት አጋንንት ይለምድና የሌሊት ደንበኛው ያደርገናል፡፡

እዚህ ላይ አንድ መረሳት የሌለበት ነገር አለ፡፡ አንዳንዴ ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) በሰይጣን ፈተና ብቻ ላይከሰት ይችላል፡፡ ምናልባት ከምንጠቀማቸው ምግብና መጠጥ እንዲሁም ከሥጋ ባህርያችን ሊከሰት ይችላል፡፡ ምክንያቱም ሰውነታችን ሲስማማው በራሱ ጊዜ ፈሳሽ ሊወጣ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ ተፈጥሮ ነው፤ ምንም ማድረግ አይቻልም በጸጋ መቀበል ነው፡፡ ለምሳሌ ማታ ትኩስ ነገር ሙቅ፣ሻይ አብዝተን የምንጠጣ ከሆነ በዘር ከረጢጣችን ያለው አባለ ዘር በራሱ ጊዜ ሊፈስ ይችላል፡፡

ተወዳጆች ሆይ በተአምረ ማርያም ላይ እንደሰማችሁት በሕልመ ሌሊት የተፈተነው ወጣት መነኩሴ ሕልመ ሌሊት ሳይሆን በሥጋው ምክንያት ሞት የመጣበት ስለመሰለው ‹‹የፍትወትን ጣዕም ዛሬ ቀምሰሻልና ወዮልሽ›› በማለት አምርሮ እራሱን ጠልቶ ወደ እመቤታችን አንብቶ ቢማጸናት እመቤታችን ተገልጣ ፈተናውን አርቃለት፣በእጆችዋም ምልክት አድርጋለት ከሕልመ ሌሊት ተላቆ በሰጠችው ሐብተ ፈውስ ብዙ ድንቆችን አድርጎ ነበር፡፡ እኛም ወለላይቱ እመ ብርሃን በሕልመ ሌሊት የሚፈትነንን አጋንንት በጸሎቷ እንድታስርልን፣እንድታርቅልን ከተማጸናት በእውነትም ይህን ፈተና፣ይህን መናጢ ታርቅልናለች፡፡

❤ ?

ተወዳጆች ሆይ ሕልመ ሌሊት ከሚከሰትብን ምክንያቶች ዋና ዋናዎችን ከዚህ በታች እናያለን፡፡

1ኛ/ በአጋንንት ይከሰታል

በጣም የሚገርመው በሕልመ ሌሊት (ዝንየት) የተፈተናችሁ እስቲ ልብ በሉ፡፡ ወደ መንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ሳትገቡ በዓለም ሳላችሁ ብዙም አይከሰትም፡፡ ቢከሰትም ለአቅመ-አዳምና ለአቅመ ሔዋን በደረስንበት ወቅት በሥጋ ባህሪያችን ይከሰታል፡፡ ወደ መንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ገብተን በተግባር መኖር ስንጀምር ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) በተደጋጋሚ ይመታናል፡፡ በተለይ ወንዶችን ቋሚ ደንበኞች ያደርገናል፡፡

ወዳጆቼ አጋንንት ጸበል እንዳንጠመቅ፣ ቤተ ክርስትያን ገብተን ጸሎት እንዳናደርስ፣ ከመለኮታዊው ማዕድ እንዳንቋደስ/ቅዱስ ቁርባን እንዳንቀበል/ ከሱባኤ ዋሻ ለማስወጣት ከሚጠቀምበት ዋንኛ ማሰናከያ መፈተኛው ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ነው፡፡ አባቶቻችን ‹‹ተጻቦዖ›› ይሉታል ‹‹ተጻብዖ›› ማለት ቃሉ የግዕዝ ሲሆን መጣላትን ያመለክታል፡፡

እኛ ሀገር ሰላም ብለን በተኛንበት ሰይጣን በማናየው መልኩ በሕልመ ሌሊት ስለሚጣባንና እኛ የማንፈልገውን ፈቃደ ሥጋ በማሳየት ፈትኖን ከሰውነታችን ፈሳሽ እንዲወጣ ስለሚያደርግ ‹‹ተጻብዖ›› ብለውታል፡፡ በእውነት ከዚህ በላይ ምን ጸብ አለ? ሰው የማይገላግለን፣ሰው የማይደርስልን፣ጮኸን የማናመልጠው ጠብ፡፡

ተወዳጆች ሆይ በሱባኤ ላይ ሆነን አጋንንት በሕልመ ሌሊት ቢፈትነን ሱባኤያችን አይፋረስም፡፡ ሕልመ ሌሊት ስለመታን ሱባኤያችን አይቋረጥም፡፡ ምናልባት በዋሻ ውስጥ ሱባኤውን የያዝን ከሆንን ለአንድ ቀን ከደጅ እንሆናለን አልያም ሰውነታችንን ታጥበን ተመልሰን ልንገባ እንችላለን፡፡

ይህን የሚወስነው የገዳሙ የአባቶች ሥርዓት ነው፡፡ ስለዚህ በሱባኤ ጊዜ በሕልመ ሌሊት በተደጋጋሚ ብንፈተን ሊደንቀን አይገባም፡፡ ይልቁንም ከአጋንንቱ ጋር በስውርና በገሃድ እየተዋጋን ስለሆነ ደስ ሊለንና በጸሎት ልንዋጋው ይገባል፡፡

ሰይጣን ሕልመ ሌሊትን (ዝንየትን) ለጸሎት ማስታጎያነት ይጠቀምበታል፡፡ ሌሊት ጸሎት ካስለመድን ከመነሳታችን በፊት ሕልመ ሌሊት ይመታናል፡፡ ከዛ በኋላ ተነስተን መጸለይ ይከብደናል፡፡ ከሰውነታችን ፈሳሽ ስለወጣ፤ ጥሩ ስሜት ስለማይሰማን ‹‹ጠዋት ታጥቤ እጸልያለሁ›› በማለት ጸሎታችንን እናስተጓጉላለን፡፡

ለዚህ መፍትሄው በፍፁም ጸሎታችንን አለመተው ነው፡፡ በዚያ በሌሊት ሙሉ ሰውነትን መታጠብ ስለሚከብድ ከቻልን ፈሳሽ የወጣበትን እርጥበት የተሰማንን ቦታ ታጥቦ መጸለይ፡፡ ሴቶችም አንቀጸ ሥጋችሁን አሊያም እጃችሁን በመታጠብ ጸሎታችሁን መቀጠል፡፡

ሰይጣን የራሳችንን ሰውነት እየተጠየፍን ጸሎት እንድንተው ነውና የሚሻው በምንም ምክንያት ጸሎት መተው የለብንም፡፡ እንኳን በሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ተመትተን ቀርቶ በጥሩ ሰዓት ማናችውንም ንፁሆች አይደለንም፡፡ የሚገርመው የማያፍረው ሰይጣን በሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ቤተክርስትያን ገብቶ ይፈትነናል ማለት ሳይሆን፤ እኛ ላይ ያለው አጋንንት በስውር ለዚህ ፈተና ሊዳርገን ይችላል፡፡

ቤተ ክርስትያን ለንግሥ አዳር ስንሄድ አባቶች አትተኙ የሚሉን አንድም ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ሊመታንና ሊፈትነን ስለሚችል ነው፡፡ ለአንድ ቀን ሌሊት ቤተ-ክርስትያን ጊዜያችንን በጸሎት ብናሳልፍ ካልሆነ ማህሌቱንና ሰዓታቱን ብንሰማ ይበልጥ ጥቅም ስላለው አለመተኛቱ ይመረጣል፡፡

2ኛ/ የዝሙት መንፈስ ካለብን

ተወዳጆች ሆይ የዝሙት አጋንንት ያው አጋንንት ቢሆንም ከሌሎቹ አጋንንት የሚለው በተልዕኮው ነው፡፡ የዝሙት አጋንንት ሰዎችን በዝሙት ማጥመድና መጣል፣ከቅድስና ሕይወት ሰዎችን ማግለል ነው፡፡ የዝሙት መንፈስ ካለብን ይበልጥ ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) ሊፈትነን ይችላል፡፡ የዝሙት መንፈስ ማለት በልቦናችንና በአእምሮአችን ዝሙትን በማሰብና ሲከፋም ወደ መፈጸም የሚያደርሰንና ከፈጣሪ የሚያጣላን እርኩስ መንፈስ ነው፡፡ የዝሙት መንፈስ በተለይ ባላገቡ ወጣቶች ላይ ይጸናል፡፡ አሁን አሁን ግን ያገቡትም የዚህ መንፈስ ተጠቂ እየሆኑ ነው፡፡


ወዳጆቼ ወጣቱ በዝሙት መንፈስ በተለያየ መንገድ ሊጠቃ ይችላል፡፡ አንዱ ተፈጥሮአችንን በመጠቀም ነው፡፡ ይህ ማለት ወደ እሳትነት ዕድሜ ክልል በምንገባበት ጊዜ የሥጋ ባህሪያችንን በመጠቀም የዝሙት መንፈስ ሊጠናወተን ይችላል፡፡ ይህም የሚሆነው ወንዶች ዓይናችን ወደ ሴቶች፣ ሴቶችም አይናችን ወደ ወንዶች ማማተር፣ በልዩ ፈቃድ መመኘትና ልባችንም ፈቃደ ሥጋን ለመፈጸም በሚከጅልበት ሰዓት ውሻ በቀደደው አንዲሉ የዝሙት መንፈስ ወደ ውስጣችን ይገባል፡፡ በዚህ መልኩ ውስጣችን ገብቶ ለዓመታት ከተቀመጠ በኋላ በተደጋጋሚ ቤተ-ክርስትያን ለመሄድ በተዘጋጀንበት ጊዜና በሱባኤ ላይ ፈተናውን በግልፅ ይጀምራል፡፡ ሳናውቅ በድብቅ ገየባው የዝሙት መንፈስ በግልጽ ይፈትነናል፡፡

ሌላው በዓለማዊ ሕይወት በምንኖርበት ጊዜ የተለያዩ ዝሙት ተስቃሽ ፊልሞችን በምንመለከትበትና መጽሐፍቶችን በምናነብበት ጊዜ መንፈሱ ሳናውቀው ወደ ውስጣችን ይገባና፤ በኋላ ሁሉን ትተን በመንፈሳዊነት ወደ ቤተ-ክርስትያን መገስገስ ስንጀምር በሕልመ ሌሊት (በዝንየት) በመፈተን ከቤተ-ክርስትያን ያስቀረናል፣ በፈተናም ያስመርረናል፡፡ ውድ አንባቢያን ፊልም ማየትና መጽሐፍት ማንበብ ኃጢኃት ባይሆንም የምናየውን ፊልምና የምናነበውን መጽሐፍ መምረጥ ይገባል፡፡ ጸያፍ እና ሥጋና ነፍስን የሚያሳድፍ ፊልም/ቨዲዮ/ ከሆነ ድብን ያለ ኃጢአት ነው፡፡

3ኛ/ ስንታበይ

አንዳንድ ጊዜ ምናልባት የዝሙት ሐሳብ ሲጠፋልን እራሳችንን እንደ ንፁህ በምንቆጥርበት ጊዜ ወይም ወደ ብቃት ደረጃ የደረስን አድርገን ስናስብ፤ ይህ መታበይ ነውና በትንሹ ጽድቃችን እራሳችንን ከፍ እንዳናደርግና ለራሳችን ልዩ የጽድቅ ቦታ እንዳንሰጥ እግዚአብሔር ሊገስጽን እንዲህ አይነት ፈተና ይመጣብናል፡፡

በመታበይ ውስጥ ያለን ሰዎች ሕልመ ሌሊት (ዝንየት) በሚመታን ሰዓት የኃጢአተኝነትና የመርከስ ስሜት ስለሚሰማን ራሳችንን ዝቅ በማድረግ ስለምንወቅስ እግዚአብሔር እንዲህ ዓይነት መንፈስ እንዲኖረን ስለሚሻ በዚህ መልኩ ሊያስተምረን ይችላል፡፡

በአንድ ወቅት ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችን በሰውነቱ ያደርገው የነበረውን ቅንዋት እንዲሰጠው ጠየቀው፡፡ ጌታም እጅግ ይወደው ስለነበረ ሰጠው፡፡ ዮሐንስም የጌታን ቅንዋት በሰውነቱ ቢያደርገው ፍፁም ድንግልና እንደ መላእክት ንፁህነት ተሰማው፡፡ ጌታም የተሰማውንና ያሰበውን ስላወቀ ወዳጄ ዮሐንስ ሆይ ‹‹ንጹህ ማነው?›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹ጌታ ሆይ! አንተ እና እኔ›› አለ፡፡

ጌታም ወዳጁ ዮሐንስ በመታበይ እንዳይወድቅበት ስላሰበ ሌሊት በሕልመ ሌሊት ፈተነው፡፡ ጠዋት ሲያገኘው ‹‹አሁንስ ንፁህ ማነው?›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹ጌታ ሆይ ንፁህ አንተ ብቻ ነህ’’ አለው፡፡ ዮሐንስም ሰው ምንም ቢመረጥ ንፅህና የባህሪ ገንዘቡ ለጌታችን ብቻ እንደሆነ በመመስከር እራሱን ዝቅ በማድረግ ተምሮበታል፡፡

ከዝሙት አጋንንት እና ከዝንየት በተጨማሪ በሕልመ ሌሊት የሚፈትነን አጋንንት የትኛው ነው?

ሀ/ ሴት ዓይነ ጥላ

ተወዳጆች ሆይ ሴት ዓይነ ጥላ ያለችበት ወንድ በሕልመ ሌሊት መከራውን ነው የምታበላው፡፡ ዓይነ ጥላዋ ስለምትቀናና ስለምትወደው ሌሊት እየመጣች በተኛበት ትገናኘዋለች፡፡ እጅግ የሚያጸይፈው ደግሞ ሴት ዓይነ ጥላ ወንድን የምትፈትነው በእናቱ፣በእህቱ በአክስቱ፣በዘመዱ፣በሥራ ባልደረባው፣በሚያውቃት እና በማያውቃት ሴት እየተመሰለች በሕልመ ሌሊት ትመታዋላች፡፡ አንዳንዱ ላይ ባስ ስትል በእንስሳት እየተመሰለች ትፈትነዋለች፡፡

ብዙ ወንዶች ሌሊት በተኙበት ከሴት ጋር ገሃድ የሚመስል ግንኙነት ሲፈጽሙ ቀለል ስለሚያደርጉት፤ ባስ ካለም ፈተና እንጂ ሴት ዓይነ ጥላ መሆንዋን አያውቁም፡፡ ዓይነ ጥላዋ ወንድን በሴት አምሳል እየመጣች ሁሌ የምትፈትነው ከሆነ የችግሩ ሰለባ የሆነው ሰው በመንፈሳዊ ሕይወቱ ታዝለዋለች፣ ጸሎት ታስተወዋለች፣ ከቤተ-ክርስትያን፣ ከጸበል፣ ከንግሥ ታስቀረዋለች፣ በሆነው ባልሆነው ዘሩን በማፍሰስ ዘሩን ደካማ ታደግበታለች፡፡ በዚህም የመውለድ እድሉን ታጠብበታለች ሲብስም ልጅ እንዳይወልድ ታደርገዋለች፣ለመካንነት ትዳርገዋለች፡፡

ለ/ ወንድ ዓይነ ጥላ

ወንድ ዓይነ ጥላ ያለባቸው ወይም የሚያንዣብብባቸው ሴቶች በሕልመ ሌሊት ይመታሉ፡፡ የሴቶች ከወንዶች የሚለየውና የሚከፋው ዓይነ ጥላው እንደ ባል አድርጓቸው እጮኛና ትዳር እንዳይዙ ከማድረጉ ባሻገር ሌሊት እየመጣ በሚገናኛቸው ወቅት ዓይነ ጥላዊ መርዙን በማህጸናቸው ውስጥ በማስቀመጥ እንደ ጽንስ ሆኖ ሊቀመጥ መቻሉ ነው፡፡

በዚህም ሴቶቹ እጮኛ አይዙም፣ትዳር አይመሠርቱም ምናልባት ትዳር ቢይዙም ትዳራቸውን በተለያየ ምክንያት መበጥበጡ እንዳለ ሆኖ ማህጸናቸውን በመዝጋት ለልጅ አልባነት ሊዳርጋቸው ይችላል፡፡ ማህናቸውና አፍረታቸው ላይ በመቀመጥም የሩካቤ ፍላጎታቸውን በመግደል፣የሴትነት ስሜታቸውን በማጓደል ደመ ቀዝቃዛ ያደርጋቸዋል፡፡

ወዳጆቼ ወንድ ዓይነ ጥላው ልክ ወንዶቹን እንደሚፈትነው ሁሉ ሴቶቹንም በአባታቸው፣በወንድማቸው፣በአጎታቸው፣በቅርብ ዘመዳቸው፣በሚያውቁትና በማያውቁት ሰው እየተመሰለ ይገናኛቸዋል፡፡ ዓይነ ጥላውም ይህንን ልምድ ያደርገውና ሴቶቹን የሌሊት መጠቀሚያው ያደርጋቸዋል፡፡

ዓይነ ጥላው አንዳንዶቹን ገና ብቅ ሳይሉ፣ምኑንም ሳይለዩ ከሕፃንነታቸው ጀምሮ ይገናኛቸዋል፡፡ ሌሎቹን ደግሞ ለአቅመ ሄዋን ሲደርሱ መገናኘት ይጀምራል፡፡ ሲብስበት ካገቡ በኃላ ባል እያላቸው እየመጣ ይገናኛቸዋል፡፡ አላፍር ሲል ደግሞ እድሜ ሲገፋ፣ስሜት ሲጠፋ እየመጣ ይገናኛቸዋል፡፡ በዚህም ለሕልመ ሌሊት ይዳርጋቸዋል፡፡

ሐ/ ሴት ዛር

ሴት ዛር ያለችበት ወንድ ልክ እንደ ዓይነ ጥላው ሁሉ ሌሊት እየመጣች ወንዱን ትገናኘዋለች፡፡ ሴት ዛር ከዓይነ ጥላ የሚያከፋት ምንም ሴት ዛር ብትሆን ቀኒታ ስለሆነች ጾታ አትመርጥም፡፡ ወንዱን ለሕልመ ሌሊት እና ለሩካቤ ሥጋ ስንፈት ትዳርጋለች፡፡ ሴቶችን ደግሞ ሌሊት እየመጣች በመደበት ከባላቸው ጋር ሩካባቤ እንዳይፈጽሙ፣በባላቸው ዘንድ እንዳይወደዱ፣እንዲጠሉ፣ለሩካቤ ሥጋ መስእብ እንዳይኖራቸው ታደርጋለች፡፡

ዓይነ ጥላ በተለይ ሴት ዛር ያለችበት ወንድ መንፈሷ የሕልመ ሌሊት ሰለባ ከማድረጓም ባሻገር አካላዊ እና ስሜታዊ ጉዳት ታደርስበታለች፡፡ ይህም ወንዱ እስኪቱ/ብልቱ/ ለግንኙነት ዝግጁ እንዳይሆንና እስኪቱ እየተሸበሸበ ወደ ፍሬው ማህደር እንዲገባ ታደርጋለች፡፡ በቀላሉ እስኪቱን ታመነምናለች፡፡

መ/ ወንድ ዛር

ወንድ ዛር ያለባት ሴት ልክ እንደ ወንድ ዓይነ ጥላ ሁሉ ሴቷን ሌሊት እየመጣ ይገናኛታል፡፡ አንድ ሴት ሌሊት እየመጣ የሚገናኛት ወንድ ዓይነ ጥላ ይሁን ሴት ዓይነ ጥላ በምን ትለያለች ካልን ወንድ ዛር ከሆነ ሁሉም በሕልሟ ያለ ፈቃድዋ በግድ እያስገደደ እያስፈራራ ነው የሚገናኛት፡፡ የማታውቀው ኃይለኛ ወንድ በግድ ሲገናኛት ታያለች፡፡

የወንድ ዛር ከዓይነ ጥላው የሚከፋው ሴቷን እንደ ሕጋዊ ባል አድርጎ ማስቀመጥ፣ አብሯት ሌሊት በሕልሟ በመማገጥ መኖር ነው ዓላማው፡፡ ወንድ ዛር ያለባቸው ሴቶችም እጮኛ አይዙም፣ ትዳር አይመሠርቱም፣ ትዳር ቢይዙም ዛሩ ማሕፀናቸው ላይ ቁጭ ብሎ ልጅ እንዳይወልዱ ያደርጋል፡፡ ቢያረግዙም ጽንሱን በደም በመምታት ሊያስቀርድ ይችላል፡፡ እንዲሁም ዛሩ አፍረታቸው ላይ በመቀመጥ፣ ስሜት ቀስቃሽ ገላቸው ላይ በመቆናጠጥ ስሜት አልባ ያደርጋቸዋል፡፡ ሩካቤ ሥጋ ቢፈጽሙም ምንም ስሜት እና ደስታ የላቸውም፡፡

ወዳጆቼ በአንድም በሌላ ከዝሙት አጋንንት ሌላ ሴት ዓይነ ጥላ፣ ወንድ ዓይነ ጥላ፣ ሴት ዛር፣ ወንድ ዛር ካለብን የሕልመ ሌሊት ሰለባ ነው የምንሆነው፡፡ እነዚህ አጋንንት በሥጋዊም በመንፈሳዊም ሕይወታችን የሚያደርሱብን የሕይወት መቃወስ እንዳለ ሆኖ ለሕልመ ሌሊት ይዳርጉናል፡፡ ወገኖቼ ሕልመ-ሌሊት (ዝንየት) በተደጋጋሚ ሲፈትነን እግዚአብሔር እንደተወን ቤተ-ክርስትያን እንዳንገባ፣ እንዳልተፈቀደልን መቁጠር የለብንም፡፡ ይልቁን ፈተና እንደሆነ አውቀን አጋንንቱን ልንዋጋ ይገባናል፡፡

ተወዳጆች ሆይ ሱባኤ ስንገባ ወንድ ሴት ሳይል በሕልመ ሌሊት ምናልባት የሚፈትነን አጋንንት ስለሚኖር እረሳችንን ለፈተና ዝግጁ አድርገን ልንጀምር እንጂ በአጋንንት ፈተና ልንደናበር አይገባል፡፡

❤ ?

1ኛ/ ጸሎት

ሕልመ ሌሊት የሚያስቸግረን ከሆነ ማታ የእለት ውዳሴ ማርያም ከበረታን ከመዝሙር ዘጠና ጋር ጸልየን መተኛት፡፡ እመቤታችንን የዝንየት አጋንንቱን እንድታስርልን እንድታርቅልን መማጸን፡፡ ያኔ በሌሊት በተቃራኒ ጾታ እየተመሰለ የሚፈትነን የሕልመ ሌሊት አጋንንት (ዝንየት) ሲርቀን በሰላም መኖር እንጀምራለን፡፡ ወዳጆቼ ብርቱ ጸሎት እንኳን ከሕልመ ሌሊት ከገሃነመ እሳት ይታደገናልና በርትተን እንጸልይ፡፡ ማታ ማታ ውዳሴ ማርያም፣አርጋኖን የቻልነውን ያህል ብንጸልይ የእመቤታችን ጥበቃ እናገኛለን፡፡

2ኛ/ ሕልመ ሌሊት እንደመታን ተመልሶ አለመተኛት

ብዙዎቻችን ሕልመ ሌሊት ሲመታን ተስፋ በመቁረጥ ተመልሰን በዛው እንተኛለን፡፡ ይሄ ድርጊታችን አጋንንቱን ከማስደሰቱም በላይ ለነገ የልብ ልብ ይሰጠዋል፡፡ እኛ በሕልመ ሌሊት ምክንያት ጸሎቱን ትተን ‹‹ጠዋት ታጥቤ እጸልያለሁ›› በሚል ስንፍና ከተኛን አጋንንቱ እየደጋገመ እየመታን ሕልመ ሌሊቱን ጸሎት ለማስታጎያ ያደርግብናል፡፡

ስለዚህ ሕልመ ሌሊት እንደ መታን ፈጥነን በመነሳት ከቻልን ሰውነታችንን መታጠብ ካልቻልን አንቀጸ ሥጋችንን በመታጣብ ጸሎታችንን መጸለይ፡፡ ወዳጆቼ ሕልመ ሌሊት እንደ መታን ተነስተን ታጥበን በመጸለያችን የነገ የአጋንንቱን ውጊያ በር እንዘጋበታለን፡፡ አጋንንቱ በሕልመ ሌሊት የሚመታን አንድም እንዳንጸልይ ስለሆነ እኛ ደግሞ በተቃራኒ ከጸለይን አጋንንቱ ይርቀናል፡፡

3ኛ/ ማታ ውኃ አብዝቶ አለመጠጣት

ሕልመ ሌሊትን ለማስታገስ አንዱ መፍትሔ ማታ ውኃ አብዝቶ አለመጠጣት ነው፡፡ ይህንን ከመጻሕፍተ መነኮሳት ሁለተኛው የሆነው ፊልክስዮስ ‹‹አካልን የሚያደርቅ፤ከሕልመ ሌሊት፣ከዘር መፍሰስ የሚከለክል፤በመዓልት ኃልዮ ኃጢአትን የሚያጠፋ እንደ ውኃ ጥም የለም፡፡ ምንም ቢጾሙ፣ምንም ከምግብ ቢያከፍሉ አብዝቶ ውኃ ከጠጣ አይጠቅምም፡፡ ምነዋ ትለኝ እንደ ሆነ ሆዱ ቂብ ትላለች›› /ፊልክ.ክፍል 3 ተስእ 38/

ውኃ ማታ አብዝቶ መጠጣት ዘር በቀላሉ እንዲፈስ ያደርጋል፡፡ አባቶቻችን በሕጋዊ ጋብቻ ያሉትን ባለ ትዳሮች ‹‹ሩካቤ ሥጋ ከመፈጸማቸው ከ30 ደቂቃ በፊት ንጹህ ውኃ ጠጡ›› የሚሉት በግንኙነት ጊዜ በሰውነት በቂ ውኃ ካላ የወንድ ዘር በቀላሉ ወደ ሴቷ ማህፀን ስለሚደርስ ነው፡፡ ውኃ ለወንድ ዘር ተሸካሚ ነው፡፡ ውኃው ነው የወንድን ዘር እንደ መርከብ በመሸከም ከማህፀን የሚያደርሰው፡፡ ስለዚህ ማታ ማታ ውኃ አብዝቶ አለመጠጣት ትኩስ ነገርም አለማዘውተር ይመረጣል፡፡

4ኛ መስገድ

ሕልመ ሌሊት አዘውትሮ የሚፈታተነን ከሆነ ስግድት ላይ መበርታት፡፡ በተለይ ማታ ከመተኛታችን በፊት እራሳችንን በስግደት ቀጥቅጠን መተኛት፡፡ በስግደት የደከመ ሰውነት ላይ አጋንንት የበላይነት አይኖረውም፡፡ ስግደት ከእነዚህ ዓይነት አጋንንታዊ ጾር የምንርቅበት እና መፍትሔ የምናገኝበት ስለሆነ መቼም ስግደት ባይሆንልንም መስገድ መልመድ ይገባናል፡፡

5ኛ/ መጠንቀቅ እና ማማከር

ተወዳጆች ሆይ እራሳችንን ለፍትወት እና ለዝሙት ከሚያጋልጡን ነገሮች የምንርቅ ከሆነ አጋንንቱ በእኛው ስህተት ለሕልመ ሌሊት አይዳርገንም፡፡ እንዲሁም ፈተናው ሲደጋገምብን ሲበረታብን አባቶችን በግል በመፍትሔው ዙርያ ማመከርና የሚሉንን መስማት እና መተግበር፡፡
ወዳጆቼ አጋንንት ወንድ ሴት ሳይል በሕልመ ሌሊት መፈተኑን አይተውም፡፡ ስለዚህ እኛ በጾም፣በጸሎት በስግደት መዋጋቱን ልንተው አይገባም፡፡

‹‹ከእመቤታችን በጸሎት መልስ የምናገኝባቸው ጠቃሚ መንገዶች›› ከሚለው መጽሐፌ ተወስዶ ብዙ አዳዲስ ሐሳቦች ተጨምሮበት ተጻፈ፡፡

ነሐሴ/1/15 ዓ.ም

አዲስ አበባ

        "ሐዋርያት በሰበሰቡአት በአንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን እናምናለን" ጸሎተ ሃይማኖት !!!!!!
23/01/2023









"ሐዋርያት በሰበሰቡአት በአንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን እናምናለን" ጸሎተ ሃይማኖት !!!!!!

👉ዕጣን ምንድነው? በቅድስት ቤተክርስቲያን ለምን ይጨሳል? መቼ ተጀመረ?መፅሐፍ ቅዱስ ስለ እጣን ምን ይላል ???ዕጣን በበረሃ ከሚበቅል እንጨት ወይም ዛፍ የሚለቀም ሙጫ ነው:: በቤተ መቅደስ...
04/04/2022

👉ዕጣን ምንድነው? በቅድስት ቤተክርስቲያን ለምን ይጨሳል? መቼ ተጀመረ?
መፅሐፍ ቅዱስ ስለ እጣን ምን ይላል ???

ዕጣን በበረሃ ከሚበቅል እንጨት ወይም ዛፍ የሚለቀም ሙጫ ነው:: በቤተ መቅደስ እንዲታጠን በእግዚአብሔር ታዘዘ።

እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው :- ‘’ጣፋጭ ሽቱ ውሰድ የሚንጠባጠብ ሙጫም ውሰድና ….. በጨው የተቀመመ ንጹሕና ቅዱስ ዕጣን አድርገው ከዚያም አንተን በምገናኝበት በመቅደሱ ውስጥ በታቦቱ ፊት ታኖረዋለህ:: እርሱም የቅዱሳን ቅዱስ ይሁንላችሁ::’’ ስለዚህ በሙሴ ዘመን ተጀመረ::

ስለ እጣን የመፅሀፍ ቅዱስ ማስረጃ:-

ዕጣን የምስጋና እና የእርገተ ጸሎት ምሳሌ ነው፡፡ ከጸሎታችንም ጋር ወደ እግዚአብሔር ፊት ይወጣል፡፡ “የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ ራእ. 8:4፡፡

ነቢዩ ዳዊት ስለ ዕጣን እንዲህ ብሏል ”አቤቱ ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ እጅ መንሳቴም እንደሰርክ መስዕዋት ትሁን ::’’ መዝ 140:2)

* ጌታችን ሲወለድ ሰብአ ሰገል ከገበሩት ውስጥ አንዱ ዕጣን ነው:: ማቴ 2:11

‘’በዕጣንም ጊዜ ህዝቡ ሁሉ በዉጭ ቆመዉ ይጸልዩ ነበር፡፡ ‘’ሉቃ 1:10

‘’መጽሀፉንም በወሰደ ጊዜ አራቱ እንሰሶችና ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በበጉ ፊት ወደቁ: እያንዳዳቸዉም በገናንና የቅዱሳን ጸሎት የሆነ ዕጣን የሞላበትን የወርቅ ዕቃ ያዙ፡፡’’ራእ 5:8

‘’ሌላም መለአክ መጣና የወርቅ ጥና ይዞ በመሰዊአዊ አጠገብ ቆመ: በዙፋኑም ፊት ባለዉ በወርቅ መሰዊያ ላይ ለቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እንዲጨምረዉ ብዙ እጣን ተሰጠዉ::’’ ራእ 8:3

ፍርድህን ለያዕቆብ: ህግህንም ለእስራኤል ያስተምራሉ: በፊትህ ዕጣንን: በመሰዊያህም የሚቃጠል መስዕዋት ይሠዋሉ፡፡’’ዘዳ 33:10

‘’ጽንሃ’’
ጽንሃ የእጣን ማሳረጊያ ወይም ማጠኛ ነው።
ሦስት ሰንሰለቶች አሉት:: ሰንሰለቶቹ ሶስት መሆናቸው የሚስጢረ ሥላሴ ምሳሌ ነው። በሰንሰለቶቹ ላይ ቢያንስ አስራ ሁለት (12) ቢበዛም ሃያ አራት (24) ሻኩራዎች ይኖሩታል። ‘’ሻኩራ’’ ማለት ሶስቱ ሰንሰለቶች ላይ ያሉት ክብ ነገሮች ናቸው:: የሻኩራዎቹ ቁጥር አስራ ሁለት (12) መሆኑ የሐዋሪያት ምሳሌ ነው።

ሃያ አራት (24) መሆኑ ደግሞ የሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ምሳሌዎች ናቸው ። ከስሩ እጣኑ የሚቀመጥበት ሙዳይ የመሰለ ክፍል የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ሲሆን: መለኮት ከሥጋዋ ሥጋ ነፍሱዋ ነፍስ ነስቶ ሰው መሆኑን ያመለክታል። ፍሙ የጌታችን የመለኮትነቱ ምሳሌ ሲሆን እጣኑ እንደሚቃጠልና መዓዛው ሁሉን እንደሚያውድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ብዙዎች ኃጢያት ራሱን መስዋዕት በማድረግ አቅርቦ ዓለሙን ሁሉ ማዳኑን ያሳያል ።

የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት: የመላእክት ጥበቃና የቅዱሳን ምልጃ አይለየን:: ፔጁን ለወዳጅ ዘመድዎ ሼር በማድረግ ስለ ቅድስት ቤተክርስቲያን የሚተላለፉ መልእክቶችን እና ትምህርቶችን በመከታተል ከበረከቱ ይቋደሱ ስለ ቅድስት ቤተክርስቲያን ያልዎትን ግንዛቤ ያሳድጉ ።

ወስብሀት ለእግዚአብሔር !!!!!
ይቆየን !!!!!!!

  መጋቢት አምስት በዚችም ቀን ተአምራቱና ትሩፋቱ እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነ ቅዱስ አባት ተጋዳይ አባ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የእረፍቱ ቀን መታሰቢያ ሆነ፡፡ ይህም...
13/03/2022





መጋቢት አምስት በዚችም ቀን ተአምራቱና ትሩፋቱ እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነ ቅዱስ አባት ተጋዳይ አባ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የእረፍቱ ቀን መታሰቢያ ሆነ፡፡ ይህም ቅዱስ አባት በተወለደባት ቀን ድንቅ የሆነ ስራን ሰራ ተነስቶ ከእናቱ እቅፍ ወርዶ ከጨለማ ወደ ብርሀን ላወጣኸኝ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን እያለ ለስላሴ ሰግዷልና ምስጋናም አቅርቧልና።

ህፃኑም ሶስት አመት በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር መልክተኛ ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ህፃኑን ከእናቱ እቅፍ አንስቶ ብዙ ባህታውያን ወዳሉበት ገዳም ወስዶ በደጅ አኖረው ወደ አበምኔቱ ወደ አባ ዘመደ ብርሀንም ገብቶ ስለ ህፃኑ እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ ነገረው።

በዚያን ጊዜም ነገሩ እውነት እንደሆነ ይረዳ ዘንድ አባ ዘመደ ብርሀን ተነስቶ ወደ ደጅ ወጣ። መልአኩም እንደ ነገረው ህፃኑ ከበር ተቀምጦ ፈገግታን ተሞልቶ አገኘው። እጅግም ደስ ብሎት ለእግዚአብሄር ሰገደ ህፃኑንም አንስቶ ሳመው ታቅፎም ወደ በአቱ አስገባው።

በፍቅር በስነስርአት አሳደገው። የዳዊትን መዝሙርና ቤተ ክርስቲያን የምትቀበላቸውን መፃህፍት ሁሉ ብሉይንና ሀዲስን አስተማረው። ከዚያም በኃላም ክህነት ይሰጠው ዘንድ ስሙ አብርሀም ወደሚባል ጳጳስ ወሰደው ጳጳሱም በአየው ጊዜ ደስ አለው።የዲቁና ማእረግንም ሾመው እንደ ቀዳሜ ሰማእት እስጢፋኖስም ፀጋንና ሞገስን የተመላ ሆነ።

ከጥቂት ቀኖች በኃላም በጌታችን ትእዛዝ ቅስና ተቀበለ። በፆም በፀሎት በስግደት በብዙ ትጋትም እየተጋደለ በበረሀ ውስጥ ብቻውን ኖረ። በበረሀም ብዙ ዘመናትን ሲኖር ነፍሱን "ነፍሴ ሆይ እወቂ በእግዚአብሔር ፊት ራቁትሽን ትቆሚ ዘንድ እንዳለሽ እንግዲህስ ፅኚ በርቺ ታገሺ!" ይለት ነበር። ቆዳው ከዐጥንቱ እስቲጣበቅ ያለ መብልና ያለ መጠጥ በእንዲህ ያለ ግብር በገድል ተጠምዶ ኖረ።ከእፅዋት ፍሬዎች ወይም ከእንጨት ስሮች አልተመገበምና ለስጋውም የሚጠቅም ምንም ምን ምክንያት አልፈለገም።

ለገብረ መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር እንዲህ አለው ከእንግዲህ በአለም ካሉ ሰዎች ከካህናት ከመነኮሳት ወይም ከምእመናን ህዝባውያን እንዳያውቁህ አደርግልሀለሁ።እንዳንተ ካሉ በቀር አንተ ራስህ ብትፈቅድ እንጂ መላእክትም ይጎበኙሀል። የብርሀን ሰረገላም ይሁንልህ መድረስ ወደምትሻበት ሁሉ ብረር እኔንም ማየትና በፈለግህ ጊዜ ከአባቴና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በሶስትነቴ ታየኛለህ።አሁንም ወደ ኢትዮጵያ ምድር ሂድ በዚያም ከደይን የምታወጥቸው ነፍሳት አሉህ አለው።

ከዚህም በኃላ ስልሳ አንበሶች ስልሳ ነብሮች በፊት በኃላ አጅበውት ወደ ኢትዮጵያ ምድር ተጓዙ። የእግዚአብሔር መልእክተኛ ቅዱስ ገብርኤልም ከአንበሶችና ከነብሮች ጋር በነፋስ ሰረገላ አሳፍሮ ይመራው ነበር። ወደ ምደረ ከብድም አደረሰው ከዚያም ወደ ልዩ ተራራ ወደ ደብረ ዝቋላ ወሰደው።

አባታችንም በባህሩ ቁሞ ምስራቁን ምዕራቡን ሰሜኑን ደቡቡን አራቱን ማእዘን ተመለከተ።የኢትዮጵያ ሰዎች የሚሰሩትን ኃጢአታቸውን በአይኖቹ ፊት የተገለጠ ሆኖ አየ። በራሱም ተዘቅዝቆ ተወርውሮ ወደ ባህሩ ውስጥ ገባ እሊህን የእጅህ ፍጥረቶች የሆኑትን ካልማርካቸው ከእዚህ ባህር እንዳልወጣ በእግሮቼም እንዳልቆም በህያው ስምህ እምላለሁ እያለ ማለ እንዲሁም ሆኖ አርባ ቀን አርባ ሌሊት ኖረ።

ስምህን የጠራውን መታሰቢያህን ያደረገውን እምርልሀለሁ የሚል ቃል በመልአክ አማካይነት ወደ አባታችን መጣ። አባታችንም መልአኩን መላውን የኢትዮጵያን ሰው ካልማረልኝ ከዚህ ባህር አልወጣም አለው መልአኩም ከአጠገቡ ሄደ።

አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም በዚያ ባህር ውስጥ መቶ ዓመት ኖረ ስጋው ሁሉ አለቀ ደሙም በባህሩ ውስጥ ፈሰሰ አጥንቶቹም እንደበረዶ ነጭ ሆነው ታዩ። አጋንንትም ከአራቱ ማእዘን በየቀኑ ሰባት መቶ ሽህ ሶስት መቶ ሽህ እየሆኑ በመምጣት በቀስታቸው ይነድፉታል እስከ መቶ አመትም አጥንቶቹን በሻፎ ድንጋይ ይፍቁታል ይህን ሁሉ መከራ በትእግስት ሲቀበል ኖረ።

ከዚህም በኃላ ጌታችን ወደርሱ መጥቶ ከባህሩ ዳር ቆመ። አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስንም መላውን የኢትዮጵያ ሰው ምሬልሀለሁና ተነስተህ ውጣ አለው ያንጊዜም ወጣ አጥንቶቹም እንደ ወንፊት ቀዳደሰ የተበሳሱ ሆነው ተገኙ ጌታም ዳሰሰውና ጤነኛ አደረገው ወደ ምድር ከብድም ሰደደው።

ከዚያም ወደ ላይ ወጥቶ ከፀሀ ከሰማይ በታች እስከ ሰባት አመት ኖረ። ዳግመኛም ወደ ምድረ ከብድ ተልኮ እንደ አምድም የተተከለ ሆኖ ሰባተረ አመት ቆሞ ኖረ። ወደ ሰማይም ሲመለከት ቅንድቦቹን አልከደነም ራሱንም ወደ መሬት ዝቅ አላደረገም ነበር እጆቹም ወደ ሰማይ ተዘርግተዋል። እነሆ ሰይጣንም በቁራ ተመስሎ መጣ አይኖቹንም ወደ ሰማይ ያንጋጠጡ ሁለቱን አይኖቹን አንቁሮ አሳወረው። እርሱ ግን ምንም ሳያጓድል እስከ ሁለት ሳምንት ድረስ እንደ ቀድሞው በመትጋት ሲፀልይ ኖረ።

ከዚህም በኃላ ሚካኤልና ገብርኤል መጥተው በፊቱ ቆሙ በሁለቱ አይኖቹ ላይም እፍ አሉበት ብርሀንም ተሰጥቷቸው እንደ ቀድሞው አዩ። ከሰማይ ታላቅ ኃይል ተሰጥቶሀልና ጠላቶችህን ትበቀላቸው ዘንድ ወደ ዝቋላ ሂድ አሉት ከዚያም መላእክት ከአጠገቡ ሄዱ። እርሱም ተነስቶ ወደ ዝቋላ ተጓዘ በጎዳናም ሲጓዝ ሶስት ሽማግሌዎች ከእንጨት ጥላ በታች ተቀምጠው አየ አባታችንም በአያቸው ጊዜ ልሰውራቸው ብሎ በልቡ አሰበ። እንርሱም ፈጥነው በእግዚአብሔር ዙፋን ተማጥነናልና ሶስታችንንም በጀርባህ እያዘልክ አንዳንድ ምእራፍ ሸኘን እንጂ አትተውን ብለው ተጣሩ። በመጣም ጊዜ ሁለመናቸውን ሽበት የከበባቸው የደከሙ ሽማግሎች ሁነው አገኛቸው አንደኛውንም አንስቶ በጀርባው አዘለው ወደ አንድ ምእራፍም አደረሰው ሽማግሌውም ከዚህ አሳርፈኝ አንተ ደክመሀል የማትበላ የማትጠጣ ስለሆንክ አለው አባታችንም ሽማግሌ ሆይ በምን አወቅከኝ አለ።

ሽማግሌውም ሂደህ ባልንጀሮቼን አምጣልኝ አለው ተመልሶ ሁለቱ ወደአሉበትም ደርሶ ሁለተኛውን ሽማግሌ በጀርባው አዝሎ ወደ ቀደመው ሽማግሌ አድርሶ አብሮ አስቀመጠው ሶስተኛም ተመልሶ ሶስተኛውን ሽማግሌ አዝሎ ሁለቱ ወዳሉበት አድርሶ በአንድነት አኖረው፡፡ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም እነዚያን አረጋውያን እናነተ ከወዴትናችሁ መአዛችሁ ልብ ይመስጣል እጅግም ደስ ያሰኛል አላቸው።እነርሱ ግን ተነስተው ቆሙ አንድ ሲሆኑ ሶስት ሶስት ሲሆኑ አንድ መሆናቸውን ገለጡለት የአባቶች አለቃ አብርሀም እንደ አየ።

ያንጊዜም የእግዚአብሔርን የጌትነቱን ክብር አየ የእሊያ አረጋውያንም ፊታቸው ተንቦገቦገ ከፀሀይና ከመብረቅ ብልጭታም ሰባት እጅ በራ አባታችንም በምስጢራት ጎርፍ የተዋጠ ሆኖ ፈራ ተንቀጠቀጠ በምድር ላይም ወደቀ። ህልምን የሚአልምም መሰለው ከዚያም ጌታችን አባታችንን አነቃውና መቶ አመት ያህል ስጋህን ሲነዱፉህ አጥንቶችህን ሲፍቁህ የኖሩ አጋንንትን ታጠፋቸው ዘንድ ወደ ዝቋላ ተራራ ውጣ አለው።

እኔ እንደ ወሰድኩህ ባለማወቃቸው በባህር ውስጥ አለ በማለት በትእቢት ላይ ናቸው ሰባቱ ሊቃነ መላእክትም ይረዱሀል መባርቅትም በፊት በኃላ ሆነው ይከተሉሀል አለው።
ያን ጊዜ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ በመብረቅ ላይ ተጭኖ በረረ እነዚያ አጋንንት ወደአሉበትም ወረደ። ደመናትም ከበቡአቸው መላእክትም በእሳት ሰይፍ መተሩአቸው በመብረቅም አጨዱ አቸው አመድም ሆነው በነፋስ በተኑአቸው። የእነዚያም አጋንንት ቁጥራቸው ሰባት መቶ ሺህ እልፍ ከአንዱ ሺህ ነበር። ከዚህም በኃላ ጌታ ክርስቶስን የካዱ ወዳሉበት ወደ ምእራብ ሀገር ወሰደው። ነገስታቱና መሳፍንቱ መኳንንቱም በሚወጡበትና በሚገቡበት ጉዳና ላይ አቆመው ጌታችንም በዚች ጉዳና ብዙ መከራ ያገኝሀል ግን በርታ ታገስ ብሎት በዚያ ተወው። በዚያን ጊዜም የአርብ ንጉስ ጣዖታቱን አስይዞ መኳንንቱን ሰራዊቱን አስከትሎ በዚያች ጎዳና መጣ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስን በጎዳና ውስጥ በተገናኙት ጊዜ ጣኦታቱ ወድቀው ተሰባበሩ።

ንጉሱም አባታችንን በአየው ጊዜ አንተ ጠጉር ለባሽ ምንድነህ ሰው ነህን አለው።አባታችንም አዎን ክብር ያለው የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያው የሆንኩ ሰው ነኝ ብሎ ለከሀዲው ንጉስ መለሰለት። ንጉሱም ዳግመኛ አባታችንን በዚያ አይሁድ በሰቀሉት ታምናለህን አለው አባታችንም በሰው ፊት አምንበታለሁ።ስለ እኔ በተሰቀለው አላፍርበትም ስለ እኔ ብቻ የተሰቀለ አይደለም ስለ አንተና ከአንተ ጋራ ስለ አሉትም ነው እንጂ ንጉስ ሆይ የዘላለም ህይወትን ታገኛላችሁ እመኑበት አለው።

ንጉሱም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ተቆጣ ሰራዊቱንም ጠርቶ በፍጥረት እሳትን አንድዱ ለተሰቀለው ለናዝሬቱ ሰው ባሪያው ነኝ የሚለውን ጠጉር ለባሽ ወስዳችሁ ጨምሩት አላቸው።የእሳቱም ነበልባል በረጅም ዛፍ መጠን ከፍ ከፍ እስከሚል አነደዱ። አባታችን ግን ንጉሱና ሰራዊቱ ሁሉ እያዩት አልፎ በፈቃዱ ወደ እሳቱ ገባ። እሳቱም እንደወንዝ ውኃ ሆነ ሰረዊቱም እጅግ አደነቁ እኩሌቶቹም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ንጉሱም ሲያደንቁ በአየ ጊዜ ፈፅሞ ተቆጣ ከሰባ ሰባት አርበኞቹ ጋራ በቁጣ ተነስቶ ያደነቁትንና ያመኑትን አንገታቸውን ቆረጠ ።

በዚያችም ቀን የተቆረጡ አርባ መቶ ሺህ ሆነው ተቆጠሩ።ንጉሱም የአባታችንን አንገት ሊቆርጥ ሰይፉን መዞ ተወርውሮ ሄደ። ያን ጊዜም ከመብረቅና ከነጎድጓድ ጋራ ታላቅ ንውፅውፅታ ሆነ ንጉሱንም ከሰራዊቱ ጋራ አጠፋው ከከሀዲው ንጉስ ጋራ የሞቱት ቁጥራቸው አራት ሺህ እልፍ ሆነ።

ጌታችንም አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስን ጠላቶችህንና የኔንም ጠላቶች አጠፋሁልህ አለው።አባተችን ግን በመብረቅ የሞቱትን ሬሳቸውን ነፍሳቸውንም መላእክተ ፅልመት ወደ ስቃይ ሲወስዱአቸው በአየ ጊዜ መድኃኒታችንን እሊህን ስሁታን ማርልኝ ሰው ስሁትና ከዳተኛ ነውና አቤቱ አንተ ግን መሀሪ ይቅር ባይ ታጋሽም ነህ አለው።አባታችንም ይህን ሲናገር ጌታችን ተሰወረ።

አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም ከዚያ ሄደ ታላቅ ገደልም አገኘ እግሮቹንም በገመድ አስሮ በገደሉ ውስጥ ተዘቅዝቆ ተሰቀለ።ሰይጣንም መጥቶ ያቺን ገመድ ቆረጣት ወደ ታችም ተወርውሮ ወረደ።ቅዱስ ሚካኤልም ቀድሞ አባታችንን ያዘው በእግርህ ላቁምህ ወይም በራስህ አለው በራሴ እቆም ዘንድ ተወኝ አለው ትቶት ሄደ።

በዚያም በራሱ ቁሞ በጥርሶቹም ደንጊያ ነክሶ እስከ ሰላሳ አመት ኖረ አንጀቱና ናላው ሁሉ እየፈሰሰ አልቆ መላ አካሉ እንደእንጨት ቅርፊት ሆነ። ከሰላሳ አመትም በኃላ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አባታችንን ገብረ መንፈስ ቅዱስ እያለ ሶስት ጊዜ ጠራው። እርሱም እነሆኝ ጌታዬ አለ ጌታችንም እነዚያን ከሀዱዎች ምሬልሀለሁ ከዚህ ተነሳ አለው።ያን ጊዜ የነከሰውን ደንጊያ ትቶ ተነሳ።ጥርሱም ተነቅሎ በድንጊያ ተተክሎ ቀረ። ክንፎችም ተሰጥተውት እየበረረ ከእግዚአብሔር ፊት ደረሰ ጌታውንም ከማርክልኝ ከስጋቸው ጋራ ተነስተው በመጠመቅ ክርስቲያኖች ይሁኑ ብሎ ለመነው። መድኃኒታችንም በሽተኞችን ልትፈውስ ሙታንን ልታስነሳ ስልጣን ሰጥቼሀለሁ አሁንም ወደተገደሉት ሄደህ በመስቀል ምልክት በላያቸው አማትብ ህይወት መድኃኒት በሆነ ስሜም አስነሳቸው አለው።ያን ጊዜም በድኖቻቸው ወዳሉበት ሂዶ አስነሳቸው አጥምቆም ክርስቲያኖች አደረጋቸው ከእርሳቸውም ሄደ።

ከዚህ ዓለም የሚለይበት በቀረበ ጊዜ እነሆ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እነሆ ተገለጠለት። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ እስከ አስራ አምስት ትውልድ የምህረት ቃል ኪዳን ሰጠው።የእድሜውም ዘመናት አምስት መቶ ስልሳ ሁለት ሲሆን በሰላም በፍቅር አረፈ። ጌታችንም ነፍሱን ተቀበለ አቅፎም ሳማት በመላእክትና በቅዱሳን ሁሉ ምስጋና አሳረጋት።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

( )

08/03/2022

ቅድስት ( የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት )
«ቅድስት» ማለት የዘይቤ ፍችው « የተቀደሰች የተለየች » ማለት ነው፡፡ ምስጢራዊ መልእክቱ ግን የምስጢረ አድኅኖት ታላላቅ ሥራውን ለመጀመር መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶሰ በገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ከቆመ ሳያርፍ፣ ከዘረጋ ሳያጥፍ የጾማት የአርብዓው ቀንና ሌሊት ልዩ የሆነችና ክብርት ጾም የምትጀመርበትን ሁለተኛ ሳምንት ከልብ ያሳስበናል፡፡ ማቴ. 4-2

ቅድሰት የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሰንበት ስያሜ ነው፡፡ ስያሜውም ከኢትዮያዊው የዜማ ሊቅ ከቅዱስ ያሬድ የተገኘ ነው፡፡ ከዚህ ሰንበት ዋዜማ ጀምሮ ስለ ዕለተ ሰንበት ቅድስና ይዘመራል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ሰንበቱን ስለ ቅድስና ልጆቿን ታስተምርበታለች ፡፡ በቅዳሴ ጊዜ የሚሰበከው ምስባክ ፤ የሚነበቡ መልዕክታት ፤የሐዋርያት ሥራ ና ወንጌል ስለ ቅድስት የሚያስተምሩ ናቸው፡፡

‹‹ቅዱስ›› ማለት ልዩ፤ክቡር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በባሕርዩ ቅዱስ ነው፡፡ ይህም ቅድስና ከማንም ያላገኘው የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ መጻሕፍትም የባሕርይ ቅድስናውን ተባብረው መስክረዋል፡፡ ባባሕርዩ ቅዱስ ስለሆነ ‹‹ቅዱስ፡ቅዱስ፡ቅዱስ›› እየተባለ ይመሰገናል፡፡( ኢሳ 6፡1-3፤40፡25 ራዕ 15፡4 ፤ 1ሳሙ2፡2-3፡፡) እኛም ቅዱስ ልጁ በሥጋ ተገልጦ እንዳስተማረን በየዕለት ጸሎታችን ‹‹ስምህ ይቀደስ›› እንለዋለን፡፡ የቅድስና ምንጭ ፡ ቅድስናን የሚሰጥ እርሱ ብቻ ነው፡፡ ‹‹ ቅዱስ›› የሚለው ቃል ለሰዎች ፡ለመላእክት ፡ ለቦታ ፡ለዕቃ፡ ለዕለታት … ቢቀጸልም ቅድስናቸው በባሕርይው ቅዱስ ከሆነው ከእግዚአብሔር የተገኘ ነው፡፡ይህም የጸጋ ቅድስና ይባላል፡፡

እግዚአብሔር ቅዱስ ስለሆነ በመልኩና በምሳሌው አክብሮ የፈጠረንን እኛም ቅዱሳን እንድንሆን ይፈለጋል፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ዳሩ ግን እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁን›› ተብሎ ስለተጻፈ የጠራቸው ቅዱስ እንደሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ ›› ያለንም ይህንን ሲያስተምረን ነው፡፡ ከመፈጠራችን አስቀድሞ መጠን በሌለው ፍቅር የወደደን እግዚአብሔር ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣን ፤ለውርደት ሳይሆን ለክብር፤ለርኩሰት ሳይሆን ለቅድስና፤ለሞት ሳይሆን ለሕይወት ነው፡፡የመፈጠራችንም ዓላማ በፊቱ በፍጹም ምግባርና ሃማኖት በመመላለስ ከእርሱ ጋር እንድንኖር ነው፡፡ ብርሃን ከጨለማ፡ ጽድቅ ከኃጢአት፡ጋር ኅብረት የለውምና ከእርሱ ጋር ለዘላለም ነግሰን ለመኖር በቅድስና መኖር ይጠበቅብናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ እግዚአብሔር ለቅድስና እንጂ ለርኩሰት አልጠራንምና ›› ያለንም ለዚህ ነው፡፡/1ተሰ 4*7/ እግዚአብሔር እኛን የፈጠረበትን አላማ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች እንዲህ ገልጾላቸዋል ‹‹ በክርስቶስ ኢየሱስ ሰማያዊ ሥፍራ በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ የባረከን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ ብሎ ካመሰገነ በኋላ ‹‹ ዓለም ሳይፈጠር በፊቱ ቅዱሳን ፡ንጹሐንና ያለነውር በፍቅር ያደርገን ዘንድ ለእርሱ መረጠን›› ኤፌ 1፡3-4 አስቀድሞ ስለወደደንና ስላከበረንም ከሌሎች ፍጥረታት በተለየ መልኩ የሚያስፈልገንን ሁሉ አዘጋጅቶ በእጆቹ ካበጀን በኋላ የሥነ ፍጥረት ዘውድ አድርጎ በገነት አኖረን ፡፡( ዘፍ 1፡26 ፤መዝ 8፡1)

የቀደመው አዳም አታድርግ የተባለውን በማድረጉ በንዝህላልነትና በስንፍና በከይሲ ዲያብሎስም ምክር ተዋረደ፡፡ በሞተ ሥጋ ላይም ሞተ ነፍስ ፤በርዕደተ መቃብር ላይ ርዕደተ ሲኦል ተፈረደበት፡ በባሕርዩ ሞት ገባበት፡ተዳደፈ፡፡ ክፉ ፍትወታት የሚያጠቁትና የሚያሸንፉት የዲያብሎስና የኃጢአት ባርያ ሆነ፡፡ በማይለወጥ ፍቅር የወደደን እግዚአብሔር ግን ጠፍተን እንድንቀር አልተወንም፡፡ በሰጠን ተስፋ፡በተቆጠረው ሱባኤና በተነገረው ትንቢት መሰረት ዘመኑ ሲደርስ በተዋህዶ ሰው ሆነ፤ የተዋረደ ሥጋችንን አከበረ፡፡ በከበረ ደሙ ዋጀን፤ከኃጢአታችን አጠበን፡፡ በእርሱ ምክንያት የእግዚአብሔር ልጆች ተባልን ፡፡ጌታችንና መድኃኒታችን ሰው የሆነውና ለመዳናችን የሆነውን ዋጋ ሁሉ የከፈለው ለእኛ ያለውን ፍቅርና ለኃጢአት ያለውን ጥላቻ ለእኛ ለማሳየት ነው፡፡ ‹‹ ነገር ግን የኃጢአትን ሥራ ይሽር ዘንድ ከእርሱ ጋር የተሰቀለውን አሮጌውን ሰውነታችን እንደሆነ ይህን እናውቃለን ›› የተባለውም ለዚህ ነው፡፡

(ሮሜ 6፡6) እኛን ወደ ቀደመ ክብራችን ለመመለስ የተከፈለውም ዋጋ ታላቅ ከሆነው የጋብቻ ምስጢር ጋር በማያያዝ እንዲህ ገልፆታል ‹‹ ክርስቶስ አካሉ ለሆነችው ቤተ ክርሰቲያን ራስዋ አዳኝዋም እንደሆነ ወንድ ለሴት ራስዋ ነውና … ወንዶችም ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን እንደወደዳት ራሱንም ስለእርስዋ ቤዛ አድርጎ እንደሰጠላት ሚስቶቻቸውን ይውደዱ፡፡ በውኃ ጥምቀትና በቃሉ ይቀድሳትና ያነጻት ዘንድ የነጻችና የተቀደሰች ትሆን ዘንድ እንጂ በላይዋ እድፈት ወይም ርኩሰት እንዳይገኝባት ቤተ ክስቲያኑን ለእርሱ የከበረች ያደርጋት ዘንድ…›› ኤፌ 5፡23-28
ስለዚህ ጌታችን በደሙ ኃጢአታችንን እንደ ቸርነቱ ይቅር ብሎናል፡፡ኤፌ 1፡7 ከእንግዲህ የራሳችን አይደለንም ፡፡ በሰውነታችንም ኃጢአትና ዐመፃን ልናደርግበት አይገባም ፡፡‹‹በዚህ በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አታንግሷት፤ለምኞቱ እሺ አትበሉት፡፡ ከሙታን ተለይቶ እንደተነሳ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጉ እንጂ ሰውነታችሁን ለኃጢአት የዐመፅ የጦር መሣሪያ አታድርጉት፤ ሰውነታችሁንም ለእግዚአብሔር የጽድቅ የጦር መሣሪያ አድርጉ››ተብለናል፡፡ (ሮሜ6፡12-13)

የተወደዳችሁ ምዕመናን እግዚአብሔር ደስ ብሎት የሚቀበለውን ህይወት ለመኖር አንፈልጋለን ፡፡ ለመሆኑ ይህ ሊሆን የሚችለው እንዴት ብንመላለስ ነው? መልሱን ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ‹‹አንደበቱን ሳይገታ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር የእርሱ አምልኮቱ ከንቱ ነው፡፡ ንጹሕ የሆነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው፤ወላጆች የሌሉአቸውን ልጆች ባልቴቶችንም በችግራቸው መጠየቅ በዓለምም ከሚገኝ ርኩሰት ሰውነትን መጠበቅ ነው፡፡››በማለት ይመልስልናል( ያዕ 1፡26-27)፡፡ በክርስቶስ ደም የተቀደሰና የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነውን ሰውነታችንን በዓለም ከሚገኝ ርኩሰት መጠበቅ የሰማያዊ ርስት ወራሾች ያደርገናል፡፡ በዓለም የሚገኘውን ርኩሰትም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹የሥጋ ሥራ ›› በማለት ገልጾታል፡፡‹‹እርሱም ዝሙት ፣ርኩሰት፣መዳራት፣ጣዖት ማምለክ፣ሥራይ ማድረግ፣መጣላት፣ ኩራት፣የምንዝር ጌጥ ፣ቅናት፣ቁጣ ፣ጥርጥር፣ፉክክር፣ ምቀኝነት፣ መጋደል፣ ስካር ፣ይህንም የመሰለ ሁሉ ነው፡፡››እነዚህን የሚያደርጉ ሰዎችም ከመንግስተ እግዚአብሔር በአፍአ ወይም በውጭ እንደሚቀሩ ሲያስረዳ‹‹አስቀድሜ እንደነገርኋችሁ ይህን የሚያደርግ የእግዚአብሔርን መንግስት አያይም›› ብሏል ( ገላ5፡19)።

በሕይወታችን ሁሉ የምግባርና የሃይማኖት ፍሬ አፍርተን መገኘት ለቅድስና የጠራንን እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት ነው፡፡እነዚህንም ነገሮች ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹የመንፈስ ፍሬዎች ›› ብሏቸዋል፡፡ እነርሱም ‹‹ፍቅር፣ደስታ ፣ሰላም፣ትዕግስት፣ምጽዋት፣ቸርነት ፣እምነት ፣ገርነት ንጽሕና ››ናቸው፡፡ገላ 5፡22 እግዚአብሔር ማደርያው ይሆን ዘንድ የመረጠውን ሰውነታችንን እርሱ የሚከብርበትን ሥራ ልናደርግበት ያስፈልጋል፡፡

‹‹በሕይወት የሚኖሩትም ስለ እነርሱ ቤዛ ሆኖ ለሞተውና ለተነሣውም እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው የሚኖሩ እንዳይሆኑ እርሱ ስለሁሉ ቤዛ ሆኖ ሞተ›› እንደተባለ በሕይወታችን ሁሉ ፋቃዱን በመመርመርና በመፈጸም በቅድስና ልንኖር ይገባናል፡፡2ቆሮ 5፡15

ቅድስናችን በኑሮአችን ሁሉ እንዲሆን ታዘናል (1ጴጥ1፡15)፡፡ ስለዚህ በተሰማራንበት የሥራ መስክ ፣በማኅበራዊ ኑራአችን ፣በምንበላው ምግብ ፣በምንለብሰው ልብስ ፣በንግግራችንና በመሳሰለው ሁሉ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኘውን በማድረግ እግዚአብሔርን በሚሞት ሥጋችን እናክብረው፡፡ ‹‹እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ የኃጢአትንም ጭንቀት ከእኛ አስወግደን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግስት እንሩጥ፡፡ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን እንከተለው፤ እርሱ ነውርን ንቆ ፣ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጧል ›› ተብሎ እንደተጻፈ ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ ተጋድሎ አድርገን ከኃጢአት ርቀት በቅድስና እንድንኖር ይገባናል(ዕብ 12፡1)። ሥጋዊ ምኞታችንንና መሻታችንን ሰቅለን አሮጌው ሰዋችንን አስወግደን ንስሐ ገብተን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብለን በቅድስና እንድናኖር ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ 4ኛ ፓትርያርክ ኾነው የተሾሙት፣ ነሐሴ 29 ቀን 1980 ዓ.ም. ሲኾን፣ በፖሊቲካዊ ግፊትና ጫና መንበራቸውን ለቀው ከሀገር ከመውጣታቸው በፊት እስከ ነሐሴ 2...
04/03/2022

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ 4ኛ ፓትርያርክ ኾነው የተሾሙት፣ ነሐሴ 29 ቀን 1980 ዓ.ም. ሲኾን፣ በፖሊቲካዊ ግፊትና ጫና መንበራቸውን ለቀው ከሀገር ከመውጣታቸው በፊት እስከ ነሐሴ 28 ቀን 1983 ዓ.ም. ድረስ ለቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ አመራር ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ከ26 ዓመታት ስደት በኋላ፣ ሐምሌ 25 ቀን 2010 ዓ.ም.፣ በስሙ በተሠየሙበት በሰማዕቱ ቅዱስ መርቆሬዎስ ክብረ በዓል ወደ ቅድስት ሀገራቸው ኢትዮጵያ መመለሳቸውን፣ ይታወቃል፡፡
ልደት

በፊት ስማቸው አባ ዘሊባኖስ ፈንታ የሚባሉት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ መርቆሬዎስ፣ በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብረ ታቦር አውራጃ በአለታ ወረዳ አረጊት ኪዳነ ምሕረት በተባለችው ገዳም ሰበካ፣ ልዩ ስሙ ማር ምድር በ1930 ዓ.ም.፣ ከብላታ ፈንታ ተሰማና ከወ/ሮ ለምለም ገሰሰ ተወለዱ፡፡

መንፈሳዊ ትምህርት

ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ፣ በተወለዱበት ገዳም መሪጌታ ላቀው ከሚባሉ መምህር፣ ንባብና ዳዊት ተማሩ፡፡ ከዚያም በኋላ አጭታን ኪዳነ ምሕረት በምትባለው ደብር ምዕራፍና ጾመ ድጓ ተምረዋል፡፡

ትምህርታቸውን ለመቀጠል ወደ ጎጃም ክፍለ ሀገር ሔደው ጎንጅ ቴዎድሮስ በተባለው ገዳም ለኹለት ዓመት ከመሪጌታ ወርቁ፣ ወደ ዋሸራ በመዛወር በቅኔ ዝነኛ ከነበሩት ከመሪጌታ ማዕበል ፈንቴ ለኹለት ዓመት በጠቅላላ በአራት ዓመት የቅኔ ትምህርታቸውን አጠናቀዋል፡፡ ከዚያም በኋላ ወደ ትውልድ ሀገራቸው ተመልሰው፣ በደብረ ታቦር አውራጃ እስቴ ወረዳ አጋጥ ደብረ ጽዮን፥ የምዕራፍ፣ ጾመ ድጓና ድጓ ትምህርታቸውን ከመሪጌታ ሙጩ አጠናቀዋል፡፡

ወደ አቋቋም ቤት በመግባት፣ መነጒዘር በሚባለው ደብር፣ ከመሪጌታ ሚናስ ለኹለት ዓመት የአቋቋም ትምህርት ተምረዋል፡፡ ከዚያም ቁት አቡነ አረጋዊ ደብር፣ ከመሪጌታ ውብ አገኝ ለአንድ ዓመት ዝማሬ መዋሥዕት ተምረዋል፡፡ ወደ ደብረ ታቦር አውራጃ ተመልሰው፣ ከጥንቱ መምህራቸው ከመሪጌታ ሙጩ ላቀ ዘንድ የድጓ ትምህርታቸውን በመቀጠል ጽፈውና አመልክተው ከጨረሱ በኋላ፣ በነፋስ መውጫ አውራጃ በታች ጋይንት ወረዳ በምትገኘው በስመ ጥሩዋ በቤተ ልሔም አራት ዓመት ቆይተው ድጓ አስመስክረው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡

የድጓ ትምህርታቸውን ካስመሰከሩ በኋላ ወደተወለዱበት ገዳም ሔደው፣ በአረጊት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ለሰባት ዓመታት ያህል ድጓ አስተምረዋል፡፡

ሥርዐተ ምንኵስናና መንፈሳዊ አገልግሎት

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ መርቆሬዎስ፣ ሥርዐተ ምንኵስናን ከመምህርነት ጋራ አጣምሮ ለመያዝ ያላቸው ፍላጎት ከፍ ያለ ስለኾነ በጣና ገዳም ዳጋ እስጢፋኖስ በመግባት ማዕርገ ምንኵስናን ከመምህር ኃይለ ማርያም(በኋላ የባሕር ዳር ቅዱስ ጊዮርጊስ መልአከ ገነት) በ1961 ዓ.ም. ከተቀበሉ በኋላ፣ በዚሁ ዓመት ማዕርገ ቅስናን፣ ከጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡

የገዳምን ሥነ ሥርዐት ይበልጥ ማጥናት ስለፈለጉ፣ በባሕር ዳር አውራጃ ልዩ ስሙ ጋሾላ በተባለ ገዳም ገብተው የገዳሙን ሥነ ሥርዐት እያጠኑና ለገዳማውያን እየታዘዙ ለኹለት ዓመት ገዳሙን ረድተዋል፡፡ በገዳሙ በነበሩበት ጊዜ፣ በጸሎተ ማኅበር፣ የልማት ሥራ በመሥራትና አቅመ ደካሞችን በመርዳት ገዳሙን አገልግለዋል፡፡

ከዚያ በኋላ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል፣ በቅዳሴና በማሕሌት እያገለገሉ ትርጓሜ ሐዲሳትንና አቡሻኽርን ተምረዋል፡፡ ዘመናዊ ትምህርታቸውንም በቅድስት ሥላሴ ትምህርት ቤት እስከ ኹለተኛ ደረጃ ተከታትለዋል፡፡ በተጨማሪም ለመምህራን፣ የተደረገውን የስብከት ዘዴ ኮርስ ለኹለት ዓመታት ተምረው የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪነት

የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ኾነው በመሾም በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ የነበረውን ችግር ተገንዝበው ለአገልጋዮች መኖሪያ ቤት አሠርተውላቸዋል፡፡ የእሑድ(የሰንበት) ት/ቤት ወጣቶችም የመሰብሰቢያ አዳራሽ ስላልነበራቸው አንድ አዳራሽ ከነሙሉ ድርጅቱ አሠርተው በመስጠት ችግራቸውን አቃለውላቸዋል፡፡ ተጀምሮ የነበረው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠናቀቅና በአካባቢው የነበሩ ምእመናንም በሰበካ ጉባኤ እንዲደራጁ ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡

ሢመተ ጵጰስና

ባላቸው በቂ የቤተ ክርስቲያን ዕውቀትና ባሳዩትም የመንፈሳዊ አገልግሎትና የሥራ ወዳድነት፣ ቤተ ክርስቲያናችን፣ ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም. ባደረገችው የ13 ኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ፣ በካህናትና በምእመናን በከፍተኛ ድምፅ ተመርጠው የኦጋዴን አውራጃ ኤጲስ ቆጶስ ኾነው ተሾመዋል፡፡

በዚህ አውራጃ፣ በጠላት ፈርሶ የነበረውን ቤተ ክርስቲያን በማሠራትና በማሳደስ፤ በጦርነት ምክንያት የተሸበረውንና የተደናገጠውን ሕዝብ በማጽናናት ስለ ኢትዮጵያ አገሩ ፍቅር በማስተማርና በማስረዳት ሐዋርያዊ ተልእኳቸውን ፈጽመዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ፣ በ1971 ዓ.ም. ወደ ጎንደር ሀገረ ስብከት ተዛውረዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በጎንደር ሀገረ ስብከት የፈጸሙአቸው ሥራዎች፡-

በወቅቱ በነበረው አለመረጋጋት፣ በጭልጋና በደባርቅ አውራጃዎች እየተዘዋወሩ ሕዝቡን በማስተማር ሰላማዊ ኑሯቸውን እንዲቀጥሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በየጊዜው በሚያሳዩት መልካም የሥራ ውጤት፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የሊቀ ጵጵስና ማዕርግ ተቀብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ራሷን እንድትችል ለማድረግ ቀዳሚ ተግባር የሚኾነው ምእመናንን በሰበካ ጉባኤ ማደራጀትና ማጠናከር ስለኾነ፣ በሀገረ ስብከት በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሰበካ ጉባኤን በማቋቋምና በማጠናከር፣ የሰንበት ት/ቤቶችንም በማስፋፋት ቅርሳቅርሶች በክብካቤ እንዲያዙ፣ ቅዱሳት መጻሕፍት፣ መጽሔቶችና ጋዜጦች ለሕዝበ ክርስቲያን እንዲደርሱ፣ የቤተ ክርስቲያን መመሪያና ደንብ ቃለ ዐዋዲ በተግባር እንዲተረጎም አድርገዋል፡፡

በጎንደር ክፍለ ሀገር የፈረሱ አብያተ ክርስቲያናት እንዲታደሱና በርከት ያሉ አዲስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲታነፁ አድርገዋል፡፡ በተለይም በደብረ ታቦር አውራጃ በእስቴ ወረዳ፡-

የአረጊት ኪዳነ ምሕረትን ቤተ ክርስቲያን በግል ገንዘባቸው ቆርቆሮ እንድትለብስ አድርገዋል፡፡
በዚሁ ወረዳ ውስጥ የምትገኘውን ደብረ ምሕረት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን፣ ከግል ገንዘባቸው ብር 9ሺሕ በማውጣት ቆርቆሮ እንድትለብስ አድርገዋል፡፡
መንፈሳዊ አዳሪ ት/ቤቶች እንዲከፈቱ፣ የካህናት ማሠልጠኛ እንዲቋቋምና ካህናት በተግባረ እድ የሚሠለጥኑበት ት/ቤት እንዲከፈት አድርገዋል፡፡
ምንም መተዳደሪያ ያልነበራቸው የአብነት መምህራንና ሊቃውንት፣ ለክህነት ከሚከፈለው ገንዘብ ደመወዝ እንዲቆረጥላቸው በማመቻቸት ሳይሰለቹና ሳይቸገሩ ሞያቸውን ለትውልድ እንዲያስተላልፉና የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችም በትምህርት አቅማቸውን እንዲያሻሽሉበት አድርገዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ለአንድ የዜማ መምህር፣ ለአንድ የቅዳሴ መምህር፣ ለአንድ ዕቃ ቤት ጠባቂ በድምሩ ለሦስት ሰዎች ከራሳቸው ደመወዝ በመክፈል ሓላፊነታቸውን እንዲወጡ አድርገዋል፡፡ በብፁዕነታቸው ሊቀ ጵጵስና፣ 43 አብያተ ክርስቲያናት ተተክለዋል፤185 አብያተ ክርስቲያናት ተሠርተዋል፡፡
የልማት ሥራዎች፤

ሀ/ በጋይንት አውራጃ በታች ጋይንት ወረዳ በምትገኘው በታላቋ ደብር ቤተ ልሔም ከአንድ በጎ አድራጊ ርዳታ በመጠየቅ በናፍጣ የሚሠራ አንድ የሞተር ወፍጮ አቋቁመው ለካህናቱና ድጓ ለሚያደርሱ ተማሪዎች ደመወዛቸውን እንዲችሉ ጥረዋል፡፡

ለ/ በደብረ ታቦር አውራጃ በእስቴ ወረዳ ሊጋባ ቅዱስ ሚካኤል በተባለው ቤተ ክርስቲያን አካባቢ አንድ የሞተር ወፍጮ በጎ አድራጊዎችን በመጠየቅ እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ አገልጋይ ካህናትም የወር ደመወዝተኛ እንዲኾኑ አድርገዋል፡፡

ሐ/ ጥንታውያን መጻሕፍት ለትውልድ እንዲተላለፉ ለማድረግ ባደረጉት ጥረት፡- ጠቢበ ጠቢባን፣ ሙሉ ሲኖዶስ፣ የቅዳሴ አንድምታ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰናቸውን ውሳኔዎች በሙሉ በብራና እንዲጻፉ አድርገዋል፡፡ በጭልጋ፣ በሊቦ፣ በደብረ ታቦር፣ በጋይንት አውራጃዎችና በእስቴ ወረዳ የችግኝ ጣቢያዎች አቋቁመው በየዓመቱ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ችግኞች በየአብያተ ክርስቲያናቱ ሰበካና ለሕዝባውያን ድርጅቶች እንዲከፋፈሉ በማድረጋቸው የተራቆቱ መሬቶች በዛፎች እንዲዋቡ ጥረዋል፡፡

መ/ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በማስፈቀድ በማኅደረ ማርያም የሐዲሳት፣ የድጓና የቅዳሴ ት/ቤት አሠርተው ለመምህራኑ ከ50 እስከ 200 ብር ደመወዝ እንዲከፈላቸው፣ ለደቀ መዛሙርቱ ድጎማ እንዲሰጣቸው አድርገዋል፡፡

ሠ/ ጥንታዊውንና ታሪካዊውን የጣና ቂርቆስ ገዳም በብር 8ሺሕ835 እንዲታደስ አድርገዋል፡፡ በጣና ለሬማ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ብር 4ሺሕ ረድተዋል፡፡ የደረሞ ቅዱስ ሚካኤልን ቤተ ክርስቲያን ብር 21ሺሕ 114 በማውጣት አሳድሰዋል፡፡ እንዲሁም ጥንታዊውን የግርቢ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በብር 8ሺሕ860 ብር እንዲታደስ አድርገዋል፡፡ በአዘዞ በሰሚ ቅዱስ ሚካኤል ወደ ካህናቱ ማሠልጠኛ የሚወስደው መንገድ በምግብ ለሥራ መርሐ ግብር እንዲሠራ አድርገዋል፡፡

በጎንደር መንበረ መንግሥት ጥበበ እድና የአዳሪ ቤቱ ዙሪያ ርዳታ በመጠየቅ ከ9ሺሕ በላይ በማወጣት እንዲሠራ አድርገዋል፡፡ በጎንደር ጉባኤ ቤትና የዶክተር አየለ ዓለሙ የመቃብር ቤት የአራቱ ጉባኤያት ሥዕል እንዲሠራበት አድርገዋል፡፡ በሊቦ አውራጃ በቆላ እብናት ለአምራቾች የኅብረት ሥራ ማኅበር ብር 15 ሺሕ ረድተዋል፡፡ በጎንደር ከተማ በአዘዞ አባ ሳሙኤል በመጠለያ ለሚረዱ ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ መምሪያ ጋራ በመተባበር የኤልክትሪክ ምጣድ ርዳታ አድርገዋል፡፡ በዳባት ወረዳ የሚገኘውን የደፍቂ ቅዱስ ሚካኤልን በብር 5ሺሕ፣ ቆማ ፋሲለደስን በብር 5ሺሕ አሳድሰዋል፡፡ ለአምስትያ ገዳም ብር 4ሺሕ፣ ለጣርክ ማርያም ብር 7ሺሕ ረድተዋል፡፡

ዐደባባይ ኢየሱስም በብር 40ሺሕ እንዲታደስ አድርገዋል፤ የድምፅ ማጉያም አስገብተውለታል፡፡ በጎንደር ዙሪያ አውራጃ ለቸንከር ተክለ ሃይማኖት ርዳታ በመጠየቅ ብር 764ሺሕ አበርክተዋል፡፡ በዚያው በጎንደር ዙሪያ ከማክሰኝት እስከ አርባያ ለመንገድ ሥራ ብር 30ሺሕ ርዳታ እንዲገኝ አድርገዋል፡፡ ከእብናት እስከ ጎሐላ ለመንገድ ሥራ የብር 6ሺሕ ርዳታ እንዲገኝ አድርገዋል፡፡

በስሜን አውራጃ ለሚገኙ ጥንታውያን ገዳማት፤ ለቤተ ሚናስ ዋልድባ ከብር 10ሺሕ በላይ፤ ለጣዕመ ክርስቶስ ብር 10ሺሕ፣ ለሰቋር ዋልድባ ብር 4ሺሕ ግምት ያላቸው የቁሳቁስ(የዓይነት) ርዳታ አድርገዋል፡፡

በጎርጎራ ገዳም በደሴተ ጣና ለሚገኙ ገዳማት፤ ለማን እንዳባ ገዳም ብር 1ሺሕ880፤ ለብርጊዳ ማርያም ገዳም ብር 1ሺሕ ለበሬ መግዣ እንዲሰጥ አድርገዋል፡፡

ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ መምሪያ ርዳታ ሰጪ ድርጀቶች በመጠየቅ አቅም በፈቀደ መጠን በተወሰኑ አብያተ ክርስቲያናት የቆዳ፣ የሽመና፣ የሹራብ ሥራ፣ የልብስ ስፌት፣ የወፍጮ ቤትና የዳቦ ቤት እንዲቋቋምና አገልግሎት እንዲሰጡ አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም ለስብከተ ወንጌል፣ ለሰንበት ት/ቤትና ለሕዝብም መሰብሰቢያ የሚያገለግሉ አዳራሾች በየአብያተ ክርስቲያናቱ አካባቢ አሠርተዋል፡፡ ሕዝቡ ንጹሕ ውኃ ማግኘት እንዲችል የውኃ ጉድጓድ በማስቆፈር ለዚሁ የሚያገለግል ሞተርና ቧምቧ እንዲያገኙ የበኩላቸውን ጥረዋል፡፡

ለሀገረ ስብከቱ ያስገኟቸው ሽልማቶች፤

የሰበካ ጉባኤ ቃለ ዐዋዲ ደንብ በትክክል እንዲፈጸም በማድረጋቸውና ሰበካ ጉባኤን በሚገባ በማደራጀታቸው፣በየዓመቱ በሚደረገው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ የሥራ ግምገማ በተደረሰበት ውጤት የጎንደር ሀገረ ስብከት ቅድሚያ ቦታ እንዲይዝ አድርገዋል፡፡

በዚህም መሠረት፡- ከ16ቱ አህጉረ ስብከት፣ ከ1975 እስከ 1977 ዓ.ም. በተከታታይ እንዲሁም በ1979 ዓ.ም. አንደኛ፤ በ1978 ዓ.ም. ኹለተኛ በመኾን በውጤታማነት እንዲሸለም አድርገዋል፡፡ ብፁዕነታቸው፣ ከዚህ በላይ ጠቅለል ባለ መልክ በተዘረዘረው ዓይነት ተልእኳቸውን በትክክል የተወጡ አባት ከመኾናቸውም በላይ በ1979 ዓ.ም. በተደረገው የብሔራዊ ሸንጎ አባላት ምርጫ በጎንደር ዙሪያ አውራጃ ምርጫ ጣቢያ ደንቢያ ከመረጠው 26ሺሕ127 ሕዝብ መካከል 17ሺሕ249 ድምፅ በማግኘት ተመርጠው ሕዝብን አገልግለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ፣ የበላዮቻቸውን መካሪ፣ የበታቾቻቸውን አክባሪ፣ በሥራ ታታሪ፣ መንፈሳዊ አባትነታቸውና ትሑት ሰብእናቸው አርኣያነት ያለው ቁጥብ አባት ናቸው፡፡

ምንጭ © ሉሌ ቋንቋዬ ነሽ ፌስቡክ ገፅ

በረከታቸው ይደርብን !!!!!!

Adresse

Ris-Orangis

Site Web

Notifications

Soyez le premier à savoir et laissez-nous vous envoyer un courriel lorsque የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መዝሙራት ፔጅ publie des nouvelles et des promotions. Votre adresse e-mail ne sera pas utilisée à d'autres fins, et vous pouvez vous désabonner à tout moment.

Contacter L'entreprise

Envoyer un message à የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መዝሙራት ፔጅ:

Partager

Type