06/03/2026
"በምዕመናን ላይ የሚደርሰው ግድያ እያበቃ ሳይሆን እየሰፋ መጥቷል" ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲዎስ
በኦሮሚያ ክልል አርሲ በተለያዩ ወረዳዎች ባለፈው እሁድ ግንቦት 23/2018 ዓ.ም 9 የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች መገደላቸውን ተከትሎብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ መግለጫ ሰጥተዋል።
ቅዱስነታቸው ዛሬ ግንቦት 26/ 2018 ዓ.ም. ባስተላለፉት መልዕክት፤ "በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ስለደረሰው አሰቃቂ ጥቃት የሰማነው በተሰበረ ልብ ነው" ብለዋል።
በዚህ ጥቃት 280 ምዕመን የተፈናቀለ ሲሆን አብያተ ተቃጥለዋል ሲል የቤተክርስቲያኗ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።
መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መቃጠሉን፣ የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን መዘረፋቸውንም ተናግረዋል።
በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት መሆኑንም አቡነ ማቲያስ ገልፀዋል።
"በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ "እስከ መቼ?" የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን ፈጥሯል" ብለዋል።
"የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅና ሰላምን የማስፈን አደራ የተጣለባችሁ የጸጥታ አካላትና በየመዋቅሩ ያላችሁ ኃላፊዎች ከምንም በላይ ታሪክ የሚጠይቃችሁ በሥልጣን ዘመናችሁ ለዜጎች ደኅንነት በምትከፍሉት ዋጋ ነውና ይህንን የጥቃት ሰንሰለት በማስቆምና ወንጀለኞችን ለሕግ እንዲቀርቡ" አሳስበዋል ።