
10/15/2025
የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ አጣብቂኝ ውስጥ ስለመግባቱ የሚያትቱት ሦስቱ ሪፖርቶች
ከሰሞኑ የኢትዮጵያ ማክሮኢኮኖሚ ላይ ስለተጋረጡ አስቸጋሪ ሁኔታዎች የሚያትቱ ሦስት የተለያዩ ሪፖርቶች ወጥተዋል። ሪፖርቶቹ ስለ ድህነት ምጣኔ መጨመር፣ የሀገሪቱ ገንዘብ የመግዛት አቅም ደካማ ከተባሉ የአፍሪካ ሀገራት ውስጥ መመደቡን እና ኢትዮጵያ የብድር መክፈያ ጊዜዋ እንዲራዘም ያቀረበችው ጥያቄ በአበዳሪዎቿ ውድቅ ስለመደረጉ የሚያትቱ ናቸው።
- የኢትዮጵያ ብር የመግዛት አቅሙ ደካማ ከተባሉ የአፍሪካ ሀገራት መገበያያ ውስጥ ስለመመደቡ ምን ተባለ?
በሀገሪቱ ያለው ፖለቲካዊ አለመረጋጋት፣ የዋጋ ግሽበት እንዲሁም የውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የብር የመግዛት አቅም መውደቁን ተገልጿል። ከሌሎች ሀገራት ጋር ሲነፃጸር የኢትዮጵያ ብር የመግዛት አቅም ደካማ ከሚባሉ 21 የአፍሪካ ሀገራት መገበያያ ውስጥ የ 18 ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በዚህ ደረጃ የኢትዮጵያ ብር ተሽሎ አሊያም በልጦ የተገኘው ከሱዳን፣ ጊኒ እና ሴራሊዮን ሆኗል። ከሐምሌ 22/ 2016 ጀምሮ ኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሬ ግብይትን በገበያ ላይ የተመሰረተ እንዲሆን አድርጋለች። ይህን ተከትሎ የብር የመግዛት አቅም በከፍተኛ ደረጃ እንዲደካም ሆኗል። ከሁለት ዓመት በፊት በባንኮች 58 ብር ገደማ ይሸጥ የነበረው 1 የአሜሪካ ዶላር ዛሬ ላይ 141 ብር እየተሸጠ ይገኛል።
- በኢትዮጵያ ያለው የድህነት ምጣኔ እንደሚጨምር የሚገልጸው የዓለም ባንክ ሪፖርት ምን ይላል?
ባለፉት 20 ዓመት፤ በሀገሪቱ ያለውን የድህነት መጠንን በመቀነስ ረገድ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን የሚጠቅሰው የዓለም ባንክ ሪፖርት ከ 4 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ 39 በመቶ የነበረው የድህነት መጠን በዘንድሮ ዓመት ወደ 43 በመቶ ሊያሻቅብ ይችላል ማለቱን ኢትዮቲዩብ ከሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል። የኮቪድ 19 ወረርሽኝ፣ በትግራይ ክልል ሲካሔድ የነበረው ጦርነት፣ የዋጋ ግሽበት ድርቅ፣ የጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ዕድገት የተጓተተ መሆን ሀገሪቱ ድህነትን ለመቀነስ እንዳትችል ያደረጓት ተግዳሮቶች መሆናቸው ተገልጿል።
አሁን ላይ ያለው የዋጋ ግሽበት በተለይ በከተማ ነዋሪዎችን ላይ ከፍ ያለ ጫና እንዳሳደረ ሪፖርቱ ይጠቅሳል። በገጠራማ የሀገሪቱ ክፍል የሚኖሩ አርሶአደሮችም ቢሆኑ ምርታቸውን “በተገደበ ገበያ” ስለሚሸጡ ገቢያቸው አነስተኛ መሆኑ ተመልካቷል። በተጨማሪም በገጠር ከሚኖረው ማኀበረሰብ 86 በመቶ የሚሆነው ጎልማሳ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ያላጠናቀቁ ናቸው ተብሏል። ይህን የሚጠቅሰው የዓለም ባንክ በተያዘው የአውሮፓውያን ዓመት በኢትዮጵያ የድህነት መጠን ሊያሻቅብ ይችላል የሚል ትንበያውን አስታውቋል።
- ኢትዮጵያ የተቀበለችውን የ1 ቢሊዮን ዶላር ብድር የመክፈያ ጊዜ እንዲራዘምላት ያቀረበችውን ጥያቄ አበዳሪዎቿ ውድቅ ስለማድረጋቸው የሚገልጸው ሪፖርት
ኢትዮጵያ በወቅቱ ያልከፈለችውን የአንድ ቢሊዮን ዶላር ዩሮ ቦንድ በተመለከተ በገንዘብ ሚኒስቴር ልዑክ እና በግል አበዳሪዎች ኮሚቴ መካከል ሲደርግ የነበረው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁ ተሰምቷል። ገንዘብ ሚኒስቴር ጥቅምት 4/2018 ዓ. ም. ባወጣው መግለጫ፤ የብድሩን አከፋፈል ሁኔታ አስመልክቶ ያለ ስምምነት መጠናቀቁን አስታውቋል። በድርድሩ ወቅት ኢትዮጵያ “ዋይት ኤንድ ኬዝ” እና “ላዛርድ” የተሰኙ የሕግ እንዲሁም የፋይናንስ አማካሪዎችን ይዞ መቅረቧን ተሰምቷል። ኢትዮጵያ ሁሉንም አበዳሪዎችን በእኩልነት ማስተናገድ የሚለውን አቋሟን በድርድሩ ወቅት እንዳንጸባረቀች ተመልካቷል።
ሁለቱ አካላት ስምምነት ላይ እንዳይደርሱ ካደረጉ ጉዳዮች አንዱ፤ የግል አበዳሪዎች ከሌሎች አበዳሪ አገራት ጋር በእኩል ዐይን መታየት አለባቸው የሚለው የኢትዮጵያ መንግሥት አቋም ነው ተብሏል። የቦንዱ ገዢዎችን የወከለው የአበዳሪዎች ኮሚቴም በአሁኑ ሰዓት ድርድሩ "ፍሬ አልባ" ደረጃ ላይ ነው የሚል ድምዳሜ ላይ መድረሱ ተሰምቷል በዚህ ሳቢያ "የሕግ እርምጃን ጨምሮ ሁሉንም አማራጮች እያጤነ" መሆኑ ተሰምቷል።