08/22/2026
ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንግሊዛዊው ደራሲና ገጣሚ ለምን ሲሳይ ሆስፒታል ገባ::
እውቁ ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንግሊዛዊው ደራሲና ገጣሚ ለምን ሲሳይ ፀጉር ቤት በተቀባው የፀጉር ቀለም ምክንያት ባሳየው ከፍተኛ አለርጂ ምላሽ ምክንያት በአስቸኳይ ሆስፒታል ገብቶ የህክምና ክትትል እየተደረገለት መሆኑ ተገለፀ።
በብራድፎርድ ከተማ በሚገኝ አንድ የፀጉር ማስተካከያ ቤት ውስጥ ለምን ሲሳይ ፀጉሩን በመስተካከል በነበረበት ወቅት ፀጉር ቆራጩ “ሙሉ በሙሉ ከተፈጥሮ የተሰራ የፀጉር ቀለም ነው” በማለት እንዲሞክረው ገፉፍቶ የቀባው አዲስ የፀጉር ቀለም ራሱን የሆስፒታል አልጋ ላይ እንዲያገኘው አድርጎታል።
ገጣሚው ፀጉሩን ተስተካክሎና ቀለም ተቀብት ከጨረሰ በኋላ ወደ ቤቱ በሚጓዝበት ወቅት፣ ከፍተኛ የመለብለብ እና የማሳከክ ስሜት እንደጀመረው ጠቅሷል። ከሰዓታት በኋላ ህመሙ እየተባባሰ የራስ ቅሉ፣ ሙሉ ፊቱ እና አንገቱ ላይ ከባድ እብጠት በማጋጠሙ በመጀመሪያ ወደ ፋርማሲስት ዘንድ በመሄድ ቅባትና ፀረ-አለርጂ መድኃኒቶችን ቢወስድም ሁኔታው ይበልጥ እየተባባሰ በመምጣቱ፥ በመጨረሻም ወደ ሆስፒታል ሊያመራ ችሏል።
የሆስፒታሉ የህክምና ባለሙያዎች እንደገለጹት፥ ገጣሚው ከደረሰበት የኬሚካል መመረዝ ምክንያት የደረሰው ጉዳት ሙሉ በሙሉ ድኖ ለማገገም ጥቂት ወራቶችን እንደሚወስድበት ገልፀውለታል። በአሁኑ ወቅት ግን በአስተማማኝ እጅ ላይ ጥሩ የህክምና ክትትል እያገኘ እንደሆነ ታውቋል።
የህክምና ባለሙያዎች ይህንን ክስተት ተከትሎ ለህዝብ ባስተላለፉት መልዕክት፥ በፀጉር ቀለሞች ውስጥ የሚገኘው PPD (Para-phenylenediamine) የተሰኘው ኬሚካል እጅግ አደገኛ የሆነ የአለርጂ ምላሽ ሊያስከትል እንደሚችል አስታውቀዋል። የጤና ዘገባዎች እንደሚያስጠነቅቁት፥ ማንኛውንም የፀጉር ቀለም ከመጠቀማችን በፊት ለ48 ሰዓታት የሚቆይ የቆዳ መሞከሪያ (Patch test) ማድረግ ግዴታ መሆን አለበት። ከዚህ ቀደም መሰል የአለርጂ ክስተቶች እስከ ህይወት ማጣት ያደረሱ የጤና እክሎችን አስከትለዋል።
ፀጉር አስተካካዩ ገጣሚውን የቀባው ቀለም ፈቃድ የሌለው ሆኖ ከተገኘ በፀጉር አስተካካዩ ላይ ፈቃድ የሌለው ምርትን በመጠቀም አደጋ ማድረስ የሚል የሙያ ቸልተኝነት ክስ ሊመሰረትበት ይችላል።
ለምን ሲሳይ በዘመናችን የስነ-ጽሁፍ ታሪክ ውስጥ ትልቅ አሻራ ያሳረፈ ድንቅ ባለቅኔ ነው። በ2012 የለንደን ኦሊምፒክ ይፋዊ ገጣሚ ሆኖ በመመረጥ ታሪክ የሰራ ሲሆን፣ በልጅነቱ በእንግሊዝ የጉዲፈቻና የማህበራዊ እንክብካቤ ስርዓት (Foster care) ውስጥ ያሳለፈውን መራራና ማንነትን የማፈላለግ የህይወት ውጣ ውረድ የከተበበት “My Name Is Why” (ስሜ ለምን ይባላል) የተሰኘው የግል ማስታወሻ መጽሐፉ (Memoir) በዓለም አቀፍ ደረጃ በብዛት ከተሸጡ መጻሕፍት (Best-seller) ተርታ ይሰለፋል።
ለምን ሲሳይ በተጨማሪም የማንችስተር ዩኒቨርሲቲ ቻንስለር በመሆን ያገለገለ ሲሆን፥ ለስነ-ጽሁፍ ላበረከተው የላቀ አስተዋፅኦ ከእንግሊዝ ንጉሳዊ ቤተሰብ የላቀ የክብር ማዕረግን ተቀብሏል።
በአሁኑ ሰዓት ከመላው ዓለም የተውጣጡ አድናቂዎቹ፣ ደራሲያን እና የጥበብ ወዳጆች ፈጣን ማገገምን እየተመኙለት ይገኛሉ።
Daniel Gebremariam