05/24/2025
♦የታመመው ማነው?♦
በስነ አእምሮ ሕክምና ዘንድ የሚታወቁ ሦስት የስነ አእምሮ በሽታ መገለጫዎች አሉ።
፩- Hallucination
፪- Illusion
፫- Delusion
የመጀመርያዎቹ ሁለቱ የተሳሳተ የሃሳብ አቀባበል/አረዳድ (Thought perception) ውጤት ሲሆን ፤ ሦስተኛው የተሳሳተ እምነት/ግንዛቤ (Thought content) ነው።
ከሌላው ሕመም በተለዬ
የስነ አእምሮ የጤና እክል ያለበትን ታካሚ ለማከም አስቸጋሪ የሚያደርገው ነገር ፤ ታማሚው መታመሙን አለማወቁ ነው።
በሽተኛው ፥ ሌሎች ሰዎች እንዲታከም ቢነግሩት እንኳን ፤ የታመሙት ሌሎች እንደሆኑ ያስባል/ያምናል። ስለዚህም በጊዜው አይታከምም። መድኃኒት ቢሰጠው በአግባቡ ለመውሰድ ፈቃደኛ አይሆንም።
ጥቂት ስለጠቀስናቸው ምልክቶች ለመነጋገር ያክል፦
♦Hallucination - የምንለው አንድ ሰው በእውነት የሌለን ነገር (Stimuli) እንዳለ አድርጎ ማዬት ፣ መስማት ፣ ማሽተት ፣ ማጣጣም ፣ መዳሰስ ነው።
ብዙ ምስሌዎችን ራሳችሁ አስባችሁ ድረሱበት።
♦Illusion - አንድ ሰው በነባራዊ ዓለም ያሉ ነገሮችን (Stimuli) የሚቀበልበት መንገድ ሲሳሳት ነው። ይህ ሰው እስክብሪቶ/Sthetoscope የያዘ ሰው መሳርያ የያዘ ሊመስለው ይችላል። የሚያለቅስ ፣ የተራበ ሰው ሲያይ የሚስቅ እና ደስተኛ የጠገበ መስሎ ይታየዋል። ምግብ ራበኝ የሚል ሰው ስልጣን ራበኝ የሚል ሊመስለው ይችላል።
♦Delusion - ይሄ ደግሞ አመክንዮ/ምክንያታዊነት ፥ ሊያሸንፉት የማይችሉ የሃሳብና የግንዛቤ ይዘት ተቃርኖ ነው። ይህም ብዙ አይነት ዘርፎች ያሉት ሲሆን የተለየ ሀይል/ውበት/አቅም አድርጎ ማሰብ/Delusion of Grandeur/, ሰዎች እየሰለሉት ፥ሊያጠቁት እየተከተሉት እንደሆነ ማሰብ /Paranoid Delusion/ ፣ ሌሎች ሳይነግሩኝ በሌሎች አእምሮ ውስጥ ያለውን ሃሳብ አውቃለሁ ማለት (Thought broadcasting) ፣ ሁሉንም ነገር ከራስ ጋር ማገናኘት (Ideas of reference) እንዲሁም Delusion of guilt ይገኙበታል።
እነዚህ ከስነ አእምሮ ጤና መታወክ መገለጫዎች ውስጥ ተጠቃሾች ናቸው።
እነዚህ ምልክቶች ያሉበት ሰው ፥ ጤናው እስኪመለስ ድረስ የስነ አእምሮ ሕክምና ማግኘት እንዲሁም የቅርብ ክትትል ያስፈልገዋል። በዚህ አረዳድ እና ግንዛቤ ውስጥ ሁኖ ሥራን በተገቢ ሁኔታ ማከናወን አይቻልም።
ያልሆነው የሆነ የሚመስለው (Hallucination)፣ የሆነውን ነገር በትክክል መተርጎም ካልቻለ(Illusion) ፣ ስለ ነገሮች ያለው እሳቤ እና እምነት ከእውነት የሚቃረን ሁኔ ከተገኘ (Delusion) ፤ ሕክምና ሳያገኙ ሥራንና ሌላን ሰው መምራት ቀርቶ ራስን መምራት አይቻልም።
በሃገራች እየሆነ ያለው ይሄው ነው።
የማይታይ ስዕል እየታየን ፣ ያልተነገረ ቃል እያደመጥን ፣ እያሸተትን ፤ በምናብ ዓለም እንኖራለን ፤ የፈጠራ ታሪክ እያወራን ከራሳችን ተጣልተን ፥ ሌሎችን እናጣላለን ፤ ፈርተን/ተሸብረን ፥ ሌሎችን እናሸብራለን።
የሚያውቁት እና የራስ የሆነን ጥያቄ ፥ እንደማያውቁት ሁኖ መገኘት።
የሚያውቁት እና ለዘመናት መፍትሔ ያላመጣን የጥያቄ መንገድ ፥ መፍትሔ የሚያመጣ ትክክለኛ መንገድ ነው ብሎ መሞገት።
የህዝብ ዓይን እና ጆሮ ነን ብለው የሚለፍፉ ሚዲያዎች ፥ የህዝቡ ዓይን ከሚያየው የህዝቡ ጆሮ ከሚሰማው በተቃራኒው ይዘግባሉ ይናገራሉ።
ብዙ ሆስፒታሎች በከፊል ተዘግተው (ሕክምና አገልግሎት መስጠት አቁመው) ፥ ብዙ ታካሚዎች እየተጉላሉ ፥ እንላለን።
የገንዘብን የመግዛት አቅም ሦስት እጥፍ (300%) ቀንሶ ፥ የ10% የደመወዝ ጭማሪ የማድረግ ሽሙጥ። (ይሄ በ290% ደመወዝ ተቀነሰ እንጅ ፥ ደመወዝ አልተጨማረም። ብር አይበላም ፤ ዓላማው መግዛት ነው።)
ይሄስ - ወዳጅ ለመምሰል መሞከር ነው።
ከድህነት ወለል በታች ቁልቁል እየወረድን ፥ በዕድገት ጎዳና ላይ እንደሆንን እናስባለን ፥ እንናገራለን።
በጽኑ ርሀብ የሚገረፍ ህዝብ ይዘን ፤ በልማት ጎዳና ላይ እንደሆንን ይሰማናል ፥ እንናገራለን ፤ ገፅታ ለመገንባት እንታትራለን።
እርዳታ እየለመንን ፥ እርዳታ እንሰጣለን።
ሰውን ከሰውነት ተራ እያወጣን ፣ እያፈረስን ፣ እያስራብን ፣ እያፈናቀልን ፣ እያራቆትን ፤ መንገድ በማስዋብ እና ኮሪደር በማልማት ሥራ ተጠምደናል።
በሃገራችን/ስለሀገራችን
ህዝቡ ዕለት ከዕለት እያጋጠመው እና እየተናገረው የሚገኘው ድምፅ ፤ የህዝብ መሪዎች ከሚሰሙት ፣ ከሚገነዘቡት ፍፁም የተለየ ሲሆን ይስተዋላል።
ችግሩ የመጣው
አውቆ የተኛ ቢቀሰቅሱት አይሰማም አይነት (Malingering) - አውቆ አበደነት ፤ ወይስ እንደታመሙ ከማያውቁበት የጤና ችግር (Hallucination ፣ Dellusion and Illusion?)
እየተወራላት የምንሰማት ኢትዮጵያ ሕዝቡ ከሚያውቃት ኢትዮጵያ ትለያለች።
ምናባዊ ዓለም
ወይስ ሌላ ሕዝቡ የማያውቃት ኢትዮጵያ ትኖር ይሆን እንጃ !
መሪዎች ስለራሱ እና ሚመሩት ህዝብ የሚናገሩት እና ተመሪው ሕዝብ ስለ ራሱ እና ስለመሪዎች የሚናገሩት በብዙው ይቃረናል።
እንደ ሃገር
ወይ እኛ ተመሪዎች (ሕዝብ) ታመናል !
ወይ መሪዎች ታምመውብናል !
እግዚአብሔር ምሕረቱን ይላክልን።
ዶ/ር ዮሴፍ