
10/01/2025
ኢትዮጵያ የኬንያን የመብራት ፈረቃ ማስቀረቷ ተዘገበ፡፡
የኬንያው ካፒታል ኤፍኤም እንደዘገበው ኬንያ ከውጭ ከምትገዛው የኤሌክትሪክ ሀይል ውስጥ ቀዳሚዋ አቅራቢ አገር ኢትዮጵያ ሆናለች፡፡
በጁን ወር 2025 ባለው መረጃ መሰረት አገሪቱ ከውጭ ከገዛችው የኤሌክትሪክ ሀይል 83 ፐርሰንቱ ከኢትዮጵያ መሆኑን ያስረዳው ዘገባው፣ በዚህ አመት ከኢትዮጵያ የተገዛው ሀይል 1274 ጊጋ ዋት ሀወር መሆኑን ጠቅሷል፡፡ በዚሁ ጊዜ ከኡጋንዳ 225 ጊጋ ዋት ሀወርና ከታንዛኒያ ደግሞ 33 ጊጋ ዋት ሀወር መብራት መግዛቷን ያስታወቀው ዘገባው ጨምሮም በዚህ አመት ኬንያ ከውጭ የገዛችው የኤሌክትሪክ ሀይል በ27 ፐርሰንት መጨመሩን አስታውቋል፡፡
ይህ የሆነው ደግሞ በኢትዮጵያና ኬንያ መካከል የኤሌክትሪክ ግዢ ስምምነት ተግባራዊ መሆን በመጀመሩ ነው ብሏል፡፡ የኬንያ የሀይልና ፔትሮሊየም ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ለዜና አውታሩ በሰጠው መግለጫ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሀይል መግዛት መቻሉ ወጪ ለመቆጠብም እንደረዳው አስረድቷል፡፡ በዚህም በአመት 10 ሚሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደሚያድንም ገልጿል፡፡
በሌላ በኩል ቢዝነስ ዴይሊ አፍሪካ የተሰኘው የኬንያ ጋዜጣ እንደዘገበው አገሪቱ በሀይል እጥረት ከፍተኛ አደጋ ውስጥ በገባችበት ወቅት ከኢትዮጵያ መፍትሄ አግኝታለች፡፡ በዘገባው በኬንያ ውስጥ የመብራት ፈረቃ የነበረ ከመሆኑም በላይ በአንዳንድ አካባቢዎች ለተወሰኑ ቀናት ጨለማ ለመሆን የሚገደዱበት ጊዜም ነበረ፡፡ ‹‹የኬንያን የመብራት ፈረቃ ኢትዮጵያ አስቀርታለች›› ያለው ዘገባው በህዳሴው ግድብ ምርቃት ላይ የኬንያው ፕሬዝደንት ዊልያም ሩቶ የክብር እንግዳ በመሆን መገኘታቸውን አውስቷል፡፡
ባለፈው ሰኔ ወር ኬንያ 200 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሀይል ከኢትዮጵያ ለመግዛት በምትችልበት ሁኔታ ላይ ስምምነት ማድረጓን ጠቅሶም ከህዳሴው ግድብ መጠናቀቅ በኋላ ተጨማሪ 200 ሜጋ ዋት ለመግዛት ጥያቄ ማቅረቧንም አስታውቋል፡፡
(Zehabesha)