06/06/2026
(ዘ-ሐበሻ ዜና) ‹‹የድሮን ድብደባ ተፈፅሞብናል›› ሲሉ ዶክተር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ገለፁ፡፡ ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝደንት ስልጣኑን በመንጠቅ የፕሬዝደንት ፅህፈት ቤቱን የተቆጣጠሩት ዶክተር ደብረፅዮን ዛሬ ባወጡት መግለጫ የድሮን ጥቃት መፈፀሙን አስታወቁ፡፡ በፅህፈት ቤታቸው በኩል ባሰራጩት መግለጫ ‹‹የብልፅግና ስርአት በትግራይ ውስጥ የሚፈፅመውን የድሮን ጥቃት ቀጥሏል፡፡
ይህም በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት አስከትሏል›› ብለዋል፡፡ ጨምረውም ‹‹የብልፅግና ስርአት የትግራይ ህዝብን ለማጥፋት ጄኖሳይድ አውጆ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ለሞት፣ ለአካል መጉደል፣ ለመፈናቀል፣ ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ውድመት ዳርጓል፡፡ በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ፊት የፈረመውን የፕሪቶሪያ ስምምነት በማፍረስም ህዝቡን ለማንበርከክ የተለያዩ ግፎችንና ኢፍትሀዊ ድርጊቶችን ሲፈፅም ቆይቷል›› ያሉት ፕሬዝደንቱ በዛሬው እለት በሰሜን ምእራባዊ ትግራይ ሽሬ አካባቢ የድሮን ጥቃት መፈፀሙን አረጋግጠዋል፡፡
በዚህ ጥቃትም በመደበኛ ስራቸው ላይ የነበሩ የትግራይ መከላከያ ሀይል ወይንም ቲዲኤፍ አባላት የሞት አደጋ እንደደረሰባቸውና የቆሰሉ እንዳሉም ገልፀው በንብረት ጉዳት መድረሱንም አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ ቀደም መንግስት የፕሪቶሪያውን ስምምነት በማፍረስ በትግራይ የተለያዩ አካባቢዎች የድሮን ጥቃት መፈፀሙን ገልፀውም ይህም የብልፅግና ስርአት ካለጦርነት መኖር እንደማይችል የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ በማጠቃለያቸውም መንግስት ቀጠናውን ወደማያቋርጥ ቀውስ ውስጥ እየከተተው መሆኑን ጠቅሰው አለም አቀፉ ማህበረሰብ ይህ ከመሆኑ በፊት እርምጃ እንዲወስድ አሳስበዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የፌዴራል መንግስቱም ሆነ የመከላከያ ሰራዊቱ ያለው ነገር የለም፣ ይህ ዜና እስከተለቀቀበት ጊዜ።