
08/09/2025
(ዘ-ሐበሻ ዜና) ዩናይትድ አረብ ኤመሬትስ ወደሱዳን የሚሄዱ መርከቦችን ማገዷን አስታወቀች፡፡ የኤመሬትስ ወደቦችን የሚያስተዳድረው ‹‹ኤዲ ፖርትስ ግሩፕ›› ዛሬ ባወጣው መግለጫ ወደፖርት ሱዳን በሚሄዱ መርከቦች በተመለከተ ከመንግስት መመሪያ እንደተሰጠው አስታውቋል፡፡
በዚህ መሰረት 1ኛ ማንኛውም ወደፖርት ሱዳን የመጓዝ እቅድ ያለው የዩናይትድ አረብ ኤመሬትስ መርከብ እንዳይንቀሳቀስ እንዲሁም 2ተኛ ማናቸውም የሱዳን የገቢና የወጪ ንግድ አካል የሆኑ ጭነቶችንና ኮንቴይነሮችን ወደፖርት ሱዳን ማድረስም ሆነ ከፖርት ሱዳን ማምጣት እንደማይቻል አስታውቋል፡፡
ይህ መመሪያ በሁሉም የአገሪቱ ወደቦች ከዛሬ አንስቶ ተግባራዊ እንደሚሆንም በጥብቅ አሳስቧል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ዩናይትድ አረብ ኤመሬትስ ከዚህ ቀደም የሱዳን አውሮፕላኖች በአገሯ እንዳያልፉ ክልከላ መጣሏ ይታወሳል፡፡ የሁለቱ አገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እዚህ ደረጃ ሊደርስ የቻለው ተቀናቃኙን ፈጥኖ ደራሽ ሀይል በጦር መሳሪያና በገንዘብ ትደግፋለች በሚል ነበር፡፡ ኤመሬትስ ግን ይህንን በተደጋጋሚ ስታስተባብል መቆየቷ ይታወቃል፡፡