11/25/2025
(ዘ-ሐበሻ ዜና) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሲንቀሳቀስ የነበረው ተቃዋሚው የቦሮ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቦዴፓ)፣ ከገዢው የብልጽግና ፓርቲ ጋር ለመዋሃድ መወሰኑ ተቃውሞ ገጠመው።
ፓርቲው ትናንት ሰኞ በመተከል ዞን ቡለን ከተማ ባካሄደው 2ኛ አስቸኳይ ድርጅታዊ ጉባኤ፣ ውህደቱን በአብላጫ ድምጽ (በ280 ድጋፍ እና በ2 ተቃውሞ) ማጽደቁን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ አመንቲ ጊሼ ለዶቼ ቬለ (DW) ተናግረዋል።
አቶ አመንቲ፣ ውሳኔው "የማህበረሰቡን ጥቅም ለማስጠበቅ" ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በርካታ የቦዴፓ አመራሮች፣ እሳቸውን ጨምሮ፣ በክልሉ መንግስት መዋቅር ውስጥ ተመድበው እየሰሩ መሆኑንና ይህ "መልካም ውጤት" ያስገኘው አብሮ መስራት ለውህደቱ መነሳሳት እንደፈጠረ አስረድተዋል።
በሌላ በኩል፣ ፓርቲውን ወክለው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆኑት ዶ/ር መብራቱ ዓለሙ ውሳኔውን በጽኑ ተቃውመዋል። ዶ/ር መብራቱ፣ ውህደቱ "የግለሰቦችን ጥቅም ለማስጠበቅ" እና ስልጣን ያገኙ አመራሮችን "ለመደለል" የተደረገ ነው ሲሉ ከሰዋል።
ጉባኤው "ትክክለኛ ያልሆነ" እንደነበር የገለጹት ዶ/ር መብራቱ፣ "የህዝቡ ጥያቄ መልስ ሳያገኝ እና ህዝቡ በጅምላ እየተጨፈጨፈ ባለበት ወቅት" ፓርቲን ማፍረስ በፍጹም ተቀባይነት የለውም ሲሉ ውሳኔውን አውግዘዋል። ዶ/ር መብራቱ ትግሉን ለማስቀጠል "ሌላ ፓርቲ ማደራጀትን" ጨምሮ አማራጭ መንገዶችን እንደሚፈልጉም ተናግረዋል።
በ2013 ዓ.ም የተመሰረተው ቦዴፓ፣ በ6ኛው ዙር ምርጫ አንድ የፌደራል ፓርላማ መቀመጫ ማሸነፉ ይታወሳል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሃሰን የውህደት ውሳኔውን ያደነቁ ሲሆን፣ ይህ ውሳኔ ይፋ የሆነው ፓርቲው ጠንካራ ድጋፍ አለው በሚባልበት ቡለን ወረዳ፣ ባለፈው ቅዳሜ ከ30 በላይ ንፁሃን ዜጎች በጥቃት በተገደሉ ማግስት መሆኑ የጉዳዩን ክብደት ይጨምራል።