12/15/2025
የሐዋሳ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ለማጠናቀቅ በሚል በሎተሪ በተሰበሰበው ገንዘብ ዙሪያ ማብራሪያ ተሰቷል። ህብረተሰቡ ጉዳዪ በገለልተኛ አካል ኦዲት ተደርጎ ለህዝብ ይፋ እንዲሆን እየጠየቀ ይገኛል
*****
የሀዋሳ ከተማ ልማት ፈንድ ምክር ቤት ኮሚቴዎች የብሔራዊ ሎቴሪ አስተዳዳር ተወካዮች፣ የሐዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ እና የከተማ አመራሮች በተገኙበት መድረክ ማብራሪያ ሰጥተዋል ።
በመድረኩ ዘርዘር ያሉ መረጃዎች የቀረቡ ቢሆንም የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ሕዝብ ግንኙት መረጃዎች መድረክ ላይ በቀረቡት ልክ ለህዝብ ከመስጠት ተቆጥቧል።
የማለዳ ሚዲያ ከውስጥ የመረጃ ምንጮቹ ባገኘው መረጃ መሠረት አጠቃላይ የታተሙ ትኬቶች 500,000 (አምስት መቶ ሺህ) መሆናቸውን፣ የተሸጡ ትኬቶች 140,000+ (መቶ አርባ ሺህ) ገደማ እንደሆነና ከዚህም 30,000,000 (ሰላሳ ሚሊየን ብር) የተሰበሰበ መሆኑን ተረድቷል።
ብሔራዊ ሎተሪ አስተዳዳር "የተወሰኑ ቀሪ ትኬቶች እኛ ጋ አሉ" ያለ ሲሆን ከሎተሪ ገንዘብ መጭበርበር ጋር ስሙ ጎልቶ ሲነሳ የቆየው የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ዘሪሁን ቃሚሶ ቀሪ የሎተሪ ትኬቶች መበላሸታቸውን ነው የገለፁት።
ተሸጠ ከተባለዉ 30,000,000 ብር ውስጥ 4,000,000 (አራት ሚሊዮን ብር) የብሔራዊ ሎተሪ ድርሻ መከፈሉን፣ 5,000,000 በሲዳማ ቡና እግር ኳስ ከለብ በኩል የተሸጠ ገንዘብ እነሱ ጋ እንደሚኖር ምክር ቤቱ ተስፋ እንደሚያደርግ፣ 19,000,000 (አሥራ ዘጠኝ ሚሊዮን ብር) በምክር ቤቱ ዝግ አካውንት ውስጥ እንደሚገኝ እና ቀሪ ገንዘብ 2,000,000 (ሁለት ሚሊዮን ብር) ለተለያዩ አስተዳዳሪያዊ ወጪዎች እንደወጣ በማብራሪያው ተመልክቷል።
ምክር ቤቱ ምንም እንኳን በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ ቢሰጥም ጠቅላላ ሂደቱ በገለልተኛ ኦዲት ተረጋግጦ በገንዘቡ ልማት ለመደገፍ የቶምቦላ ሎተሪ ለገዛው ለሰፊው ማህበረብ የተሰጠ ሕጋዊ መግለጫ የለም።
አስተይስየታቸውን ለማለዳ ሚዲያ የላኩ የህብረተሰቡ ክፍሎች ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ኦዲት ተደርጎ ለህዝብ ይፋ እንዲሆን ጠይቀዋል።
ማለዳ ሚዲያ