01/05/2026
❗️ጭንብሏ የወለቀባት ኢምፔሪያሊስቷ አሜሪካ
~~~~~~~~~~
ማናለብኝነት ነፋፍቶ ያሳበጣት የጽዮናውያኑ መከታ፣ የኢምፔሪያሊዝም ዋልታ አሜሪካ የቬንዝዌላን ሉዓላዊ ግዛት በመውረር የሃገሪቱን ፕሬዚደንትና ባለቤቱን አፍና ወሰደች። ለዚህ የአለም አቀፍ ህግጋትን በግልጽ የጣሰ የወረራ እርምጃዋ ምክንያት ያደረገችው ሀገሪቱ አደንዛዥ እፆችን ወደ አሜሪካ ትልካለች የሚል ነው። ይህንን አሜሪካ የወሰደችውን የምናለብኝ የወረራ እርምጃ ሩስያ፣ ቻይናና ኮሎምብያን ጨምሮ አንዳንድ ሃገራት ቢያወግዙም አውሮፓውያን ግን መንተባተብን መርጠዋል።ከወቀሳ ለማምለጥ ሲሉ ደግሞ ፕሬዚደንቱ ማዶሮ አምባገነን መሪ ስለሆነ ሥልጣኑ ህጋዊነት የለውም የሚልን ትርክት ለህዝባቸው ለመሸጥ ሲጋጋጡ ታይተዋል።
ትራምፕ ቬንዝዌላን በመውረርና ፕሬዚደንቷን በማፈን የመንግሥት ለውጥ ለማምጣት የተነሳበት ምክንያት መንግሥቱ አምባገነን ስለሆነ ወይንም አደንዛዥ እፅ ወደ አሜሪካ ስለሚልክ ሳይሆን ሃገሪቱ ያላትን ከፍተኛ የቤንዚን ሃብት ለመቀራመት እንደሆነ ከማንም የተደበቀ አይደልም። የአንድ ሃገር መንግሥት በምዕራባውያኑ አገላለጽ አምባገነን ስለሆነ ብቻ የወረራ ሰለባ እንዲሆን የሚፈቅድ ህግ ቢኖር ኖሮ በርካታ ሃገራት ድሮ ገና በተወረሩ ነበር። ነገር ግን ሁሉም ሰው በደንብ እንደሚያውቀው ጥቅሟን እስካስጠበቁላት ድረስ አሜሪካ ከአምባገነን መንግሥታት ጋር ወዳጅ እንጂ ፀበኛ አይደለችም። እንዲያውም በተቃራኒው ወደ ዲሞክራሲ የሚደረጉ እርምጃዎችን በማደናቀፍ ነው የምትታወቀው።
አሜሪካ በተለይ አሁን ዶናልድ ትራምፕ ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላ የዲሞክራሲ ጭንብሏን ሙሉ በሙሉ አውልቃ አስፈሪ ገጽታዋን በግልጽ ማሳየት ጀምራለች።ፍልስጤም ህዝቦች ላይ እየተፈጸመ ያለውን የዘር ፍጅት ከማሳለጥ አልፋ በግልጽ ወረራ ፈጽማለች። ኩባንና ግሪን ላንድ ያካተተ ተጨማሪ ወረራዎችን ለመፈጸምም እየዛትች ትገኛለች።
አሜሪካ በዚህ የማንአለብኝነት እርምጃዋ እያስተላለፈች ያለው መልዕክት ሃያላን አገራት ደካሞችን ያለምንም ምክንያት መውረር ይችላሉ የሚል ነው። አሜሪካ ቬንዝዌላ ላይ ወረራ ስትፈጽም ለሩሲያ ወይንም ለቻይና ወይንም ለሌሎች ሃያላን መንግሥታት እያለቻቸው ያለው “እናንተም አቅም ካላችሁ ጎረቤቶቻችሁን በወረራ ማንበርክርክ ትችላላችሁ” ነው። ይሄ መቸም ዞሮ ዞሮ ወደየት ሊያደርሰን እንደሚችል መገመት የሚያስቸግር አይመስለኝም። በአንድ ወገን በጉልበተኞች የመዋጥ አደጋ የተደቀነባቸው ሃገራት ያለባቸውን የደህንነት ስጋት ለመቅረፍ ሲሉ ለሃያላኑ ግብር የመክፈል ግዴታ ላይ እንዲወድቁ ሊያስገድድ ይችላል። በሌላ በኩል ደግሞ በተወሰነ ደረጃ ራሳቸውን የመከላከል አቅም ያላቸው ደግሞ ጡንቻዎቻቸውን ለማፈርጠም የጦር መሳርያ እሽቅድድም ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ። ይህም ሁኔታ አለማችንን እጅግ በጣም ያልተረጋጋች ያደርጋታል የሚል ስጋት አለ።
ይሄ አሜሪካ እያሳየችው ያለ መጥፎ ባህሪይ ዞሮ ዞሮ ራሷንም የሚያጠፋ ቢሆን በሂደት ግን ብዙ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል ነው። ደግሞ የጉዳቱ ሰለባዎች የሚሆኑት ሁሉም ሃገራት ናቸው። ይዘገይ ይሆናል እንጂ ማንም ከጉዳት የሚድን ሃገርም ሆነ ህዝብ የለም። ስለዚህ ይህንን ከመንገድ የወጣ ዋልጌ ድርጊት ሁሉም ሃገራት በአንድ ድምፅ ሊያወግዙት ይገባል።
🗣️ የእርስዎ አስተያየት ምንድን ነው?
አስተያየትዎን ያጋሩ! 👇
ለተጨማሪ መረጃ ቴሌግራማችንን ተቀላቀሉ
https://t.me/RNZeroFive