11/14/2025
" የበሽታዉ መንስኤ ማርበርግ ቫይረስ (Marburg Virus) መሆኑን መለየት ተችሏል " - ጤና ሚኒስቴር
የጤና ሚኒስቴር በደቡበ ኢትዮጵያ ክልል በጅንካ ከተማ የሄሞራጅከ ፊቨር (Viral Hemorragic Fever) በሽታ መከሰቱን እና የበሽታዉን ምንነት በማረጋገጥ ላይ መሆኑን መግለጹ ይታወቃል፡፡
ሚኒስትሩ በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ የበሽታዉ መንስኤ ማርበርግ ቫይረስ (Marburg Virus) መሆኑን መለየት ተችሏል ብሏል።
የዘረመል ምርመራው የተከናወነው በኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ብሄራዊ ሪፈረንስ ላብራቶሪ ነው።
መግለጫው "በዚህም የዘረመል ምርመራ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ የተገኘዉ ቫይረስ ሌሎች ምስራቅ አፍሪካ ሃገራት ላይ ከዚህ በፊት ከተከሰቱት ጋር ተመሳሳይ ዝርያ ያለዉ መሆኑ ታዉቋል" ነው ያለው።
በተጨማሪም በዛሬው እለትም አዲስ የበሽታውን ምልክት ያሳየ ወይም በቫይረሱ የተጠረጠረ ሰው ያልተገኘ መሆኑን ሚኒስትሩ ያሳወቀ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት የተለያዩ የሙያ ስብጥር ያካተተ ከፍተኛ ፈጣን ምላሽ ሰጭ ቡድን ወደ ከልሉ በመላከ በሽታዉን የመከላከል እና የመቆጣጠር ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ ብሏል።
ከነዚህም ውስጥ :-
° የማህበረሰብ አቀፍ የቅኝት ስራዎች፣
° በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ለይቶ ማከም፣
° የማህበረሰብ ግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች እና ከተጠረጠሩ ሰዎች ጋር ንክኪ ያላቸዉን ሰዎች የመለየት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተገልጿል።
በሃገር አቀፍ እንዲሁም በክልል ደረጃ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች የክስተት አስተዳደር ስርዓት (Incident Management System) ተቋሞ የፈጣን ምላሽ ስራዎችን በማስተባበር ላይ ይገኛል ተብሏል።
Hagere Infotainment